በእንግሊዝ ሀገር የቨርችዋል ግቢ ጉባኤ ተማሪዎች ተመረቁ

ከዩኬ ንዑስ ማእከል 

ነሐሴ ፩ ቀን ፳፻፲፫ ዓ.ም

ተመራቂ የግቢ ጉባኤ ተማሪዎች (በከፊል) ከአባቶች ጋር

በማኅበረ ቅዱሳን አዉሮፓ ማእከል በዩናይትድ ኪንግደም ን/ማእከል አስተባባሪነት ላለፉት ሦስት ዓመታት ተከታታይ የቤተ ክርስቲያን ትምህርት ሲማሩ የነበሩ 11 የግቢ ጉባኤ ተማሪዎች ሐምሌ 24 ቀን 2013 ዓ/ም በአባቶች ቡራኬ ተመረቁ። በለንደን ደብረ ገነት ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን አዳራሽ በተካሄደዉ በዚህ የተማሪዎች ምርቃት መርሐ ግብር ላይ ካህናት አባቶች፣ ተመራቂ ተማሪዎችና የተመራቂ ቤተሰቦች፣ ጥሪ የተደረገላቸዉ እንግዶች፣ የማኅበረ ቅዱሳን አባላት፣ ሌሎች የግቢ ጉባኤ እንዲሁም የሰ/ት/ቤት ተማሪዎች የተገኙ ሲሆን ሌሎች የአዉሮፓ ማእከል አባላት እና ታዳሚዎች መርሐ ግብሩን በዙም (Zoom) ተከታትለዋል። የአዉሮፓ ማእከል ሰብሳቢ ዲ/ን ፈንታ ጌቴ ለተመራቂዎች የ’እንኳን ደስ ያላችሁ’ መልእክት አስተላልፈዋል። በዚህም ተመራቂዎች ወደ ማኅበረ ቅዱሳን ተቀላቅለዉ የማኅበሩን አገልግሎት እንዲያግዙ ጥሪ አቅርበዋል።

ትምህርት በመልአከ ሰላም ቀሲስ አዲስ ሲሰጥ

በዚህ የምረቃ መርሐ ግብር ላይ፣ መልአከ ሰላም ቀሲስ አዲስ አበበ የለንደን ደብረ ገነት ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን አገልጋይና የስብከተ ወንጌል ኃላፊ ትምህርት ሰጥተዋል። በተጨማሪም ተማራቂዎችና የፍሬ ሃይማኖት ሰ/ት/ቤት ተማሪዎች መዝሙር ያቀረቡ ሲሆን በግቢ ጉባኤ በመምህርነት ከሚያገለግሉት አባቶች መካከል መልአከ ሣህል ቀሲስ ዶ/ር ያብባል ሙሉዓለም እና ሊቀ ኅሩያን ቀሲስ ፍስሐ ለተመራቂዎች መልእክት አስተላልፈዋል።

 

ለተመራቂዎች የመስቀል ስጦታ በአባቶች ሲሰጥ

 

ለተመራቂዎች የመስቀል ስጦታ በአባቶች አማካኝነት ተበርክቷል። በን/ማእከሉ የተተኪ ትዉልድ እና ግቢ ጉባኤ ክፍል ተወካይ ለመርሐ ግብሩ ታዳሚዎች መልእክት ያስተላለፉ ሲሆን በዚህም ለግቢ ጉባኤዉ ስኬት አስተዋጽኦ ያደረጉትን መምህራንና ሌሎች አካላትን በሙሉ አመስግነዋል። ለምረቃ መርሐ ግብሩ የቤተ ክርስቲያኑን አዳራሽ ለፈቀደው የቤተ ክርስቲያኒቱ ሰበካ ጉባኤ ጽ/ቤት ምስጋናቸዉን አቅርበዋል።

የተተኪ ትዉልድ ንዑስ ክፍል ባለፈዉ ዓመት ዕድሜያቸዉ ሰባት ዓመት እና ከዚያ በላይ የሆኑ ከሦስት መቶ በላይ የሚደርሱ ህጻናትን፣ በየዕድሜያቸዉ ለይቶ የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት በእንግሊዘኛ ቋንቋ ሲሰጥ መቆየቱን አስታዉሰዉ ትምህርቱን በተጠናከረ መልኩ ለማስቀጠል ምዝገባ እየተካሄደ መሆኑን ገልጸዋል። በግቢ ጉባኤ ንዑስ ክፍልም እንዲሁ አዳዲስ የአንደኛ ዓመት ተማሪዎችን ለመመዝገብ ዝግጅት ማጠናቀቁን ገልጸዉ ይህንን የምዝገባ መልእክት በማስተላለፍ ሁሉም አካላት እንዲተባበሩ ጠይቀዋል።

የ’ቨርችዋል’ ግቢ ጉባኤዉ በዩኬ በመጀመሩ ምክንያት የዘንድሮ ተመራቂዎች ሁሉም ከዩኬ ሲሆኑ፣ ከሁለት ዓመት በፊት ጀምሮ፣ ግቢ ጉባኤዉ በሌሎች የአዉሮፓ አገሮች ያሉ ተማሪዎችን ያካተተ በመሆኑ አሁን ላይ ወደ አዉሮፓ ግቢ ጉባኤነት ያደገ መሆኑን ገልጸዋል።