ዕረፍተ ሶልያና

በዲ/ን ዶ/ር ቴዎድሮስ በለጠ 

ጥር  21 ቀን 2010 ዓ.ም.

 

የቤተክርስቲያናችን ዓይን ሊቁ ቅዱስ ያሬድ ለአምልኮ መቅረዝ ለምስጋና ማኅቶት በሆነው የድጓ ድርሰቱ የእመቤታችንን የከበረ ዕረፍት ከዘመነ አስተርእዮ ምስጢር ጋር እያዛመደ እንዲህ አስፍሮታል።

∽†∽ “ጊዜ ዕረፍታ ለሶልያና፣ ወረደ ወልድ እም ዲበ ልዕልና፣ ጠሊሳነ ንግሥ ሶቤሃ ከደና ” ∽†∽

ድጓ: መነሻው “ድግ” ነው የሚሉ ዓይናማ ሊቃውንት “ድጋ ለቤተክርስቲያን” ብለው ድርሰቱ የተዋህዶ መደገፊያ መሆኑን ይነግሩናል። ምንጩን  ደግደገ ካለው አንስተው ድግዱግ በሚለው ደቃቅ ለማለት ስበው ረቂቅ ማለትም ነው ይላሉ ፤ እንደ ሊቃውንቱ ሀተታ ከጽሕፈቱ ረቂቅነት ከምልክቱ ብዛት የተነሣ የተሰጠው መጠሪያ ነው። በሌላ አገባብም በዘይቤው የዓመቱ መዝሙራት ተወጣጥተው ተሰብስበው ይገኙበታልና ድጓ እስትጉቡእ ወይም ስብስብ ማለትም ይሆናል።

ሊቁ በዚህ የድጓ ድርሰቱ፦ የነቢያቱን የትንቢት ማረፊያ፣ የሐዋርያቱን የስብከት መነሻ፣ የነገረ ድኅነት ጥልቅ ማብራሪያ፣ የሆነውን ነገረ ማርያምን በልዩ መንገድ ያስረዳናል። በተለይም የሥላሴ ማደሪያ የቤተ ክርስቲያን አንደበት ለሥጋ ለባሽ ሁሉ ትምክኅት የሆነች እመቤታችን በዘመነ አስተርእዮ በጥር ፳፩ ቀን የተከናወነው የከበረ “ዕረፍተ ሶልያና” በምን ክስተት እንዳለፈ እንዳንዘነጋው ሁሉን ከሚያስብ ከማይዘነጋ ልጇ እንድታማልደን እየተማጸነ ጭምር አብራርቶ ይዘግባል።

የዕረፍቷን ድርሰት ለማተት እጅግ ጥቂት መነሻ ታሪክ እናስቀድም፤

በነቢያቱ የተስፋ ትንቢትና በአበው ኅብረ ምሳሌ ስትጠበቅ የኖረች እመቤታችን የብጽአት (የስእለት) ልጅ ሆና ከአብራከ ኢያቄም ተመርጣ፣ ከማኅጸነ ሃና ተፈጥራ ፣ ከአንስተ ዓለም ተለይታ፣ ከሁሉ ልቃ፤ ወደምድራችን ስትገለጥ በወላጆችዋ ቤት ለ፫ ዓመታት ቆይታ ለቤተ መቅደስ የስእለት ሥጦታ ሆና ለ፲፪ ዓመታት  ብርሃናውያን የሚሆኑ የሰማይ ሠራዊት ቅዱሳን መላእክት ዘወትር እያረጋጓት በአገልግሎት ትጋት በተቀደሰው ሥፍራ ቅድስቲቱ በክብር ኖራለች። እንዲጠብቃት ለፃድቅ ገሊላዊ ዘመዷ ዮሴፍ ታጭታ ሳለች በብሥራተ መልአክ አምላክን ልጇ ክርስቶስን በግብረ መንፈስ ቅዱስ ጸንሳ በመውለድ ለ፴፫ ዓመት ከቤተልሔም ዋሻ ልደቱ እስከ ቀራንዮ ኮረብታ ስቅለቱ ሳትለየው አብራው ተገኘች። የዓለም መድኅን እናቱን በጎልጎታ ለወዳጁ ወንጌላዊ ዮሐንስ በእናትነት ሰጠው እርሱም ለ፲፭ ዓመታት እጠብቃት ብሎ ወስዶ ተጠበቀባት። ለአረጋዊው ፃድቅ በ፲፭ ዓመቷ በእጣ የመታጨቷን እና ለወጣቱ ሐዋርያ በ፵፭ ዓመቷ በእናትነት የመሰጠቷን በእርሱ ቤትም ፲፭ ዓመት የመኖርዋን ነኪር ኩነት የቁስጠንጥንያው ሊቅ አፈወርቅ ዮሐንስ እንዲህ አራቅቆታል።

በከመ ሰመያ እግዚእነ ለእሙ እመ ዮሐንስ በብሂሎቱ “ነያ እምከ” እንዘ ኢተወልዶ፤ ወመልአክኒ ከመዝ ሰመያ  ለእግዝእትነ ማርያም (ፍኅርትከ) እንዘ ኢየአምራ (እመቤታችን ዮሐንስን ሳትወልደው ጌታችን እናቱ ማርያምን እነኋት እናትህ ብሎ የዮሐንስ እናት እነደሆነች እንደገለጣት ሁሉ መልአኩም ኅትምት ድንግልን ዮሴፍ ‘ሳያውቃት’  እጮኛው ብሎ ጠራት)

በታማኝ ልጇ በቅዱስ ዮሐንስ በኩል የሚታመኑ ልጆችዋን ስትጠብቅ የኖረች እናት ፷፬ ዓመት ሲሆናት በፍጥረት ሁሉ የደረሰ የሥጋን ዕረፍት እንዲያገኛት በእጅጉ የሚያስደንቀው ዕለተ ሞቷ ጥር ፳፩ ቀን በ፵፱ ዓ·ም ተፈፀመ።

ደራሲው “ሞትሰ ለመዋቲ ይደሉ: ሞታ ለማርያም የአጽብ ለኩሉ” እንዳለው የሕይወት መሠረት፣ የመድኃኒት እናት፣ የፈውስ ቤት፣ ቤዛዊተ ዓለም፣ አዲሲቷ እምቦሳ፣ የደስታ መፍሰሻዪቱ፣ የነባቢው በግ እናት ያን የሥጋ ሞት እንድትቀምሰው ልጇ ከመላእክቱ ጋር ተገለጠላትና  ቅን ፍርዱን ገለጠላት፤ ለእኛም ይጥቀማችሁ ሲለን ታላቁን  ክብሯን ገለጠልን።

ይኼንን ይዞ አፈ ሊቃውንት ቅዱስ ያሬድ “ጊዜ ዕረፍታ ለሶልያና፣ ወረደ ወልድ እም ዲበ ልዕልና፣ ጠሊሳነ ንግሥ ሶቤሃ ከደና” አለ።  ⇨  ሶልያና ባረፈች ጊዜ ክብር፣ የክብርም ክብር የተገባው ወልድ ልጇ ክርስቶስ ከልዕልናው በልዕልና ወረደ እናቱን በጠሊሳነ ንግሥ በዚያን ጊዜ  ሸፈናት። “  ጠሊሳነ ንግሥ ያለው የክብሯን መንዲል የንግሥናዋን መጎናፀፊያ ነው።

ሶልያና ማናት?

ለሶልያና ስመ ተጸውኦ መነሻ ግንዱ “ሴሊኒ” የሚለው ልሳነ ጽር (የግሪክ ቃል) ነው ይላሉ የሀገራችን የሰዋስው ሊቃውንት፤ በትርጉም ሶልያና ያለውን የቅዱስ ያሬድን ስያሜ ከሴሌኒ ጋር በአቻ ፍካሬ “ጨረቃ” የሚል ትርጉም ሰጥተውት እናገኛለን።

ለአገናዛቢነቱም በዓለማችን ያሉ በስም ዙርያ መነሻ ግንዱን ታሪካዊ ይዘቱን እና አገባባዊ ትክክለኛ አጠቃቀም በሳይንሳዊ መንገድ የሚያትቱ ባለሙያዎች  “መፈክራነ አስማት” (Onomatologists or Onomasticians) ይባላሉ።  

ፍካሬ አስማት፣ የስም ትርጉም ጥናትም ( Onomastics or Onomatology) በሥሩ ሁለት ዓበይት ዘርፎች ያቅፋል፤ ይኸውም  (1) አስማተ መካን (Toponymy or toponomastics) የቦታ ስያሜዎችን የሚመረምር ሲሆን (2) አስማተ ሰብእ (Anthroponomastics) በሰዎች ስም ዙሪያ የሚያተኩር ሀተታ የሚሰጥበት በየጊዜው ለሚወጡና ለሚሰሙ መጠሪያ ስሞች በአስረጅ አስደግፎ ማብራሪያ የሚያስቀምጥ ዘርፍ ነው።

ታዲያ እነዚህ ‘ሊቃውንትም’ ቢሆን ምንጭ አልባ ፈሳሽ ሥር አልባ ግንድ እንዳይኖር ተረድተው ሶልያናን “Σελήνη” ካለው ከግሪክ ምንጩ ቀድተው “Celena” ወይም “Selene” ያለውን መነሻ ግንድ አንቅተው ለአንስት የተገባ ትርጉሙም “ጨረቃ” (The Moon) ማለት ነው አሉን። የምንጩን ምንጭ የበለጠ ለማተት ከሚያስችል ማደሪያ ሲያደርሱን ደግሞ selas (σέλας) ከሚለው ማመሳከሪያ ጋር ያጣምሩልናል ትርጉሙም ብርሃን (light) ማለት ነው። ጨረቃ እንደ ፀሐይና ከዋክብቱ ማኅደረ ብርሃንም አይደል!

እስኪ ደግሞ በእኛው ቅዱሳን ሊቃውንት እና ቅዱሳን መጻሕፍት ሀተታ የምሥጢር ባህር የትርጓሜ ማዕበል እጅግ ጥቂት እንመላለስ።  

+ አቡቀለምሲስ ዮሐንስ “ብእሲተ ሰማይ ለባሲተ ፀሐይ” እያለ በራእይ ምዕራፍ ፲፪ ላይ የተገለጠለትን ዓቢይ ትእምርት  ሲገልጥልን “ጨረቃን ተጫምታለች ከዋክብትን ተቀዳጅታለች” እያለ የብርሃን ድንኳን (ደብተራ ብርሃን) መሆኗን ያትታል።

የድጓው ባለቤትም ከድርሰቱ የአንዱን ክፍል መጠሪያ “አንቀጸ ብርሃን” በሚል ስያሜ ለሕይወት መሰላል ለመለኮት ማደሪያ እመ ብርሃን ምስጋናን ማዘጋጀቱ ቅሉ ለዚህ ነው! የፀሐይ መውጫ ምሥራቅ፣ ደጃፉ ለብርሃነ ጽድቅ እርሷ ናትና።

ዳግመኛም አማናዊቷን ጽዮን ወላዲተ አምላክን ጸወን ያደረገ የ “ሕዝበ ጽዮን” እና  “እምነ ጽዮን” ልጅ የጋስጫው ሊቅ አባ ጊዮርጊስ በሰዓታት ምስጋናው “ኮከበ ብርሃን ጽብሐዊ፣ ፀሐያ ጽድቅ አርያማዊ” የሚሆን የፍጥረት ሁሉ ገዥ ብርሃን ክርስቶስን የወለደች እናትም አገልጋይም ሆና የተገኘች ድንግል ማርያም የተጫማችው ጨረቃ የለበሰችው ፀሐይ የብርሃን መኖርያ የንጽሕና ማደሪያ መሆኑን ገላጭ እንደሆነ ሲያስረዳ  ለአሣዕንኪ ወርኅ ወለቶታንኪ ጎህ ልብስኪ ንጽሕ” በማለት ተቀኝቶላታል።

+ በነገረ ማርያም  የምናገኘው ሌላው የጨረቃ ምሥጢር ደግሞ ከእመቤታችን ፯ኛ ቀዳሚ አያቶች ከጴጥርቃና ከቴክታ የተገኙ ፷፯ ወንዶች መካከል ነገር ያላቸውን ትንቢት የተነገረላቸውንና ሱባኤ የተቆጠረላቸውን ሲነግረን ከጨረቃውም ትርጉም ሲያደርሰን ቴክታ ያየችውን ለከበረ ጴጥርቃ የነገረችውን ሕልም እንዲህ ብሎ ያሳትታል ” በህልሜ ነጭ ጥጃ ከማህጸኔ ስትወጣ ያችም ነጭ ጥጃ ሌላ ነጭ ጥጃ ስትወልድ እንዲሁ እስከ ፯ት ትውልድ ሲዋለድ ሰባተኛይቱ ጨረቃን ስትወልድ ጨረቃዋም ፀሐይን ስትወልድ አየሁ”

ይኽውም በመፈክረ ሕልም “እግዚአብሔር በምሕረቱ አይቷችኋል በሳህሉ መግቧችኋልና ፯ አንስት ጥጆች መውለዳችሁ ፯ ሴቶች ልጆች እና የልጅ ልጆች ትወልዳላችሁ ከቤታችሁ ሰባተኛይቱ ጨረቃ መውለዷም ከሰው በእጅጉ የበለጠች ከመላእክትም የከበረች ደግ ፍጥረት ትወልዳላችሁ የፀሐይ ነገር ግን አልታወቀኝም” ተብሎ ተነግሯቸው ነበርና ይኸውም ሊደርስ በፈቃደ እግዚአብሔር ሄሜን የተባለች ልጅ ወልደዋል።በዚህም የዘር ሐረግ ሰንሰለትም  ሄሜን → ደርዲ → ቶና → ሲካር → ሴትና → ሄርሜላ → ቅድስት ሀና (እማ ለእማምላክ ፯ተኛይቱ ጣዕዋ) ተገኝታለች።

ሰባተኛይቱ “ጥጃ” ሀናንም በእርግናዋ ወራት አምላክ አስቧት ጨረቃ የተባለች “አዲሲቷን እምቦሳ” የፀሐይን እናት ድንግል ማርያምን ብትጸንስ ሞቶ የነበረ የአጎቷ ልጅ “ሳሚና” በተአምር ተነስቶ ከመፈክረ ሕልም የቀረውን ፈ’ቶ እንዲህ ሲል መስክሯል “ስብሃት ለኪ ማርያም እሙ ለፀሐየ ጽድቅ ለአብ መርዓቱ ለወልድ ወላዲቱ ለመንፈስቅዱስ ጽርሃ ቤቱ ተፈስሒ”።

ይኽ ምሥጢር በሳሚና የተገለጠ ብቻ አልነበረም መላእክቱ በመንጦላእተ ብርሃን ውስጥ ሆነው የሚያመሰግኗት ‘እንዲያ’ እያሉ ነው “በሐኪ ማርያም ሐዳስዩ ጣዕዋ … አዲሲቷ እምቦሳ ላንቺ ምስጋና ይገባሻል”።

ሶልያና አዲስ እምቦሳ ከጥጆች የተገኘችና ፀሐይን ያስገኘች ጨረቃ ድንግል ማርያም ናት።

ሊቃውንቶቻችን መች በዚህ ብቻ ይብቃን ይላሉ፤ የሊቁን ስያሜ  ሲያራቅቁ በዘይቤ ረቂቁ አካላዊ ቃል ወልድ የተነበበባትን ሶልያና ትርጉም የፊደል ገበታ ማለት ነው ይሉናል “መዝገቡ ለቃል” ትባላለችና።

መልሰውም የስሟን ዝርዝር በፊደል ከ”አጽርሖተ ቃል” የተዋቀረ የእመቤታችንን ክብር የሚገልጽ መጠሪያ ስምም ያደርጉታል። እንዲህ እያሉ:-

         ሶ ✧ ሶበሰ ኪዳንኪ ምክንያተ ድኂን ኢሀሎ (ኪዳንሽ ባይኖር ምክንያተ ድኂን የለም)

          ✧ ልሳንየ ላእላእ ይሴብሀኪ (ዲዳው ትብ አንደበቴ ያመሰግንሻል)

         ያ ✧ ያንቅአዱ ሀቤኪ ኩሉ ፍጥረት(ፍጥረታት ሁሉ ወደአንቺ ያንጋጥጣሉ)

          ✧ ናሁ ተግህደ ልዕልናሃ ለድንግል፥ (እነሆ የድንግል ታላቅነቷ ተገለጠ)

ዘመነ አስተርእዮ እና ዕረፍተ ሶልያና

ዘመነ አስተርእዮ የበጎ ነገር ሁሉ ወዳጅ ክርስቶስ የጸላዔ ሰናያት የዲያቢሎስን ክፉ ሥራ ለማፍረስ መገለጡ የሚታሰብበበት ነው (፩ዮሐ ፫፥፱)። ከልደቱ እስከ ጥምቀቱ “አንሶሰወ ከመሰብእ እንደ ሰው ተመላለሰ” በሕግ ጠባይዓዊ፣ በሕግ መጽሐፋዊ ግብር ታየ በመባል ሲነገርለት የነበረ የእዳ ጽሕፈታችንን እንደሰውነቱ ረግጦ እንደ አምላክነቱ አቅልጦ ከፈለገ ዮርዳኖስ ሲደመስስ ለቤዛነት መምጣቱን በግልጥ ያስመሰክር ጀመር። ከገዳም የ፵ ቀን ቆይታ መልስ በቃና ዘገሊላም ቀዳሚ ተአምር ውኃን ወደ ወይን በእናቱ ምልጃ በመቀየር አሳይቷል። ተያይዞም አስተርእዮቱን የሚያትቱ በዓላት በምሥጢር እየተገናኙ በዚህ ዘመን ይታወሳሉ (፭ቱን ኅብስተ ሠገም ፪ቱን ዓሣት ያበረከተበት ጥር አማኑኤልን ጨምሮ)።

ሊቁ “ጊዜ ዕረፍታ ለሶልያና፣ ወረደ ወልድ እም ዲበ ልዕልና” ማለቱ በዘመነ አስተርእዮ ምሥጢር ውስጥ የማናጣት “ለቃል ርደት ዙፋን ለሥጋ ዕርገት መሰላል” የሆነችው እናቱ በዕለተ ዕረፍቷ የበለጠ አስተርእዮቱ መገለጡን ለማሳሰብ በታላቅ ልዕልናው ከልዕልናው ወደ ምድር ዳግመኛ የመጣውን የአምላካችንን አስተርእዮ ለማተትም ጭምር ነው።

ውበቷን የወደደው የሠማይ ንጉሥ ቀድሞ ለኑሮ ያደገችበትን ‘ቤት’ ፤ ኋላ ለነፍስ ያደረችበትን ‘ሥጋዋን’ ትታ እንድትከተለው ሲጠራት “ልጄ ሆይ፥ ስሚ እዪ ጆሮሽንም አዘንብዪ፤ ወገንሽን ያባትሽንም ቤት እርሺ፤ ንጉሥ ውበትሽን ወድዶአልና፥ እርሱ ጌታሽ ነውና።” (መዝ ፵፬ ፥፲) ይላታል። ወስዶም በዐረፍተ ዘመን የማይተዋት በቅድስት ትንሳኤና በከበረ ዕርገት እንደሚጎበኛት ሲያስረዳ “ወዳጄ ሆይ! ተነሺ:: ውበቴ ሆይ! ነዪ::”(መኃ. ፪፥፲፫) ሲል ትንቢቱን አናግሯል።

የጥር ፳፩ዱን “ዕረፍተ ሶልያና” አስተርእዮ ማርያም ያሰኘው በሥጋ መለየቷ በዘመነ አስተርእዮ መፈጸሙ ብቻ ሳይሆን ጌታ እልፍ አዕላፋት መላእክቱን አስከትሎ በዕረፍቷ ዕለት ተገልጦበታልናም ነው።

የዘመነ አስተርእዮ ሠርግ (ዘመነ መርዓዊ) እና ዕረፍተ ሶልያና

ዘመነ መርዓዊ ከቃና ዘገሊላው ተአምር ተያይዞ በዘመነ አስተርእዮ ማገባደጃ የሚታሰብ ወቅት ነው።

በስንክሳሩ አርኬ የተቀመጠው ሰላምታ ዕረፍቷን ከሰርግ ጋር እያዛመደ እንዲህ ያስተምረናል።

“ሰላም ለጸአት ነፍስኪ በመዓዛ ክርስቶስ ዘተነቅበ

ወመሰንቆ ማኅሌት ሐዋዝ እንዘ ያመዓርር አልባበ

ሐራ ሰማይ ብዙኃን እለ አልቦሙ ሐሳበ

እንዘ ይዜምሩ ቅድሜኪ ወመንገለ ድኅሬኪ ካዕበ

ማርያም ሞትኪ ይመስል ከብካበ፡፡”

በክርስቶስ መዓዛ ለሰቀቀው (ከዚኽ ዓለም ለተለየው) እና ልብን በእጅጉ ደስ በሚያሰኘው በመሰንቆ ጣዕመ ማኅሌት ለተከናወነው የነፍስሽ መውጣት ሰላምታ ይገባል፤ ብዙ የሚሆኑ ቁጥር የማይገድባቸው ልክ የማይወሰንላቸው የሰማይ ሠራዊት በፊትሽ እየቀደሙ ዳግመኛም ከኋላሽም እየተከተሉ ሲዘምሩ ታይተዋልና ማርያም ሆይ ሞትሽስ ሰርግ ይመስላል።

በምድር እየተሰረጉ በሰማይ የከበረውን እንዲህ ያለ ሰርግ ለማሰብ የታደሉ እንደምን የተመሰገኑ ናቸው!

በንጽሕና የኖረ ወልደ ነጎድጓድ ዮሐንስ በታላቅ ክብር ወደተመለከታት፣ ድምጹን አሰምቶ ወደተናገረላት፣ የነቢያት ሁሉ ደስታቸው ፈጣሬ ዓለማት ክርስቶስ ወደ አደረባት፣ አዲሲቷ ጽዮን፣ የአምላካችን ሀገሩ፣የመለኮት ምኅደሩ፣  በእንግዳ ሥርዓት ዕረፍቷ ሰርግ ወደተባለላት ንስቲት መርዓት (ታናሽ ሙሽራ) እንድናይ የማለዳው ምስጋናችን ሁላችንንም እንዲህ ሲል ይጠራናል

ሃሌ ሉያ ንዑ ትነጽሩ ኅበ ዛቲ መርዓት ዘሥርጉት እመ በግዕ ወዑጽፍት በዝንቱ ስብሐት ዓቢይ በከመ ይቤ ወልደ ነጐድጓድ። ዮሐንስ ድንግል ወንጹሕ ይጸርሕ እንዘ ይብል እስመ አብርሀ(ት) (ለ)ዛቲ ይእቲ። ጽዮን ሐዳስ። ሀገረ አምላክነ። ዘኃደረ ላዕሌሃ ፍሥሓ ኵሎሙ ነቢያት ቅዱሳን።”

ደገኛ መጽሐፍ በጀመረበት መጨረስ ልማዱ እንደሆነ በማሰብ እኛንም ከርቱዕ ሕሊና እንዳያርቀን እየተማፀንን ከሊቁ በረከት እንዲያሳትፈን ደጅ እየጠናን፤ መልሰን ፈልፈለ ማኅሌት ቅዱስ ያሬድን ከድጓው እንጥራው እና የሰርግ ቀን በተባለ የዕረፍቷ ዕለት ሰማያዊውን ሰርግ በዓይነ ሕሊናችን አቅርበን የሶልያናን ዕረፍት ሀተታ እንዲህ  እንቋጨው፤

ዮም ይባቤ የበቡ

ኃጢዓተ እለ ዘገቡ

በኪዳነ ድንግል ካህን ሥርየተ እለ ረከቡ

ከመ ይባኡ ለወልድኪ ውስተ ከብካቡ

የሊቁ ፍቅር ምንኛ ይደንቃል! የድንግሊቱ የአምላክ እናት “ቃልኪዳኗ” ኃጢአት ሲሰሩ ለኖሩ ሥርየተ  የሚያሰጥ “ካህን” ነው ይላል። የታመኑባት ኃጥአን በዕለተ ምጽዓት በደስታ እየዘመሩ ወደ ሰርጉ አዳራሽ የሚሻገሩባት አግዓዚት፣  ተጨንቀው ለሚጠሯት ሰማዒት ፣ ወደ ማኅደረ ነፍስ የሚደርሱባት ማዕዶት እርሷው ናትና።

በዕረፍቷ በድካመ ሥጋ በገቢረ ኃጢአት ከመባከን በንሰሀ መልሳ የዕረፍት ውኃ የለመለመ መስክ በተሰኘ “ሥጋሁ ለአማኑኤል ዘነሥአ እምእግዝእተ ኩልነ” ብለን በምንቀበለው  ቅዱስ ምሥጢር እንድናርፍ ምልጃዋ አይለየን።

ወስብሐት ለእግዚአብሔር!