የቤተልሔም እንስሳት

ታኅሣሥ 2003 , ስምዐ ጽድቅ

እንደምን ሰነበታችሁ ልጆች

ልጆች ቤተልሔምን ታውቋታላችሁ?ቤተልሔም ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተወለደባት ከተማ ናት። እና ልጆች የቤተልሔም እንስሳት ጌታችን መወለዱን በሰሙ ጊዜ እጅግ ተደስተው “ምን ይዘን እንሂድ? ምንስ እናበርክት?”በማለት በሬዎች፥በጎች፥ጥጃዎች፥ህያዎችና ሌሎች እንስሳት ተሰብስበው መወያየት ጀመሩ።


ፀሐይ ልጆቿን ጨረቃንና ከዋክብትን ጠርታ “ልጆቼ ሆይ ዛሬ ታላቅ ደስታ በኢየሩሳሌም ሀገር በቤተልሔም ከተማ ተፈጽሟል።የዓለም ፈጣሪ ጌታችን ተወልዷልና ፍጥረታት ሁሉ በደስታ የምንዘምርበት ቀን ነው።እና ልጆቼ የጥበብ ሰዎች /ሰበዓ ሰገል / ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መወለዱን ሰምተው ከሩቅ ሀገር ተነስተው መምጣት ፈልገዋልና ከእናንተ መኻከል ማነው ጎበዝ እነዚህን ክቡር እንግዶች ፈጥኖ ይዟቸው የሚመጣው?” ስትል ጠየቀቻቸው። ሁሉም ‘እኔ ልላክ እኔ ልላክ”እያሉ ሲያስቸግሯት እናታቸው ፀሐይ ዕጣ አውጥታ ለአንዷ ኮከብ ደረሳት። ዕጣ የወጣላት ኮከብ ከደስታዋ ብዛት በሰፊው ሰማይ ላይ ክብልል እያለች እየበረረች እንግዶቹ ዘንድ ደረሰች።እንግዶቹም ለታላቁ ጌታችን የምናበረክተው ስጦታ ብለው ዕጣን፥ ወርቅ፥ከርቤ ይዘውለት ሲመጡ አገኘቻቸው።ኮከቧ በጣም ደስ አላትና ቦግ ብላ በራች።ወደ ቤተልሔምም እየመራቻቸው ሔደች።


ጌታችን በተወለደባት ሌሊት በቤተ ልሔም ከተማ አካባቢ ከብቶቻቸውን ሲጠብቁ ያደሩ እረኞች ነበሩ።የጌታ መልአክ ወደእነርሱ ቀረበ። ወዲያውም ያሉበት ቦታ በብርሃን ተጥለቀለቀ። በዚህ ጨለማ የምን ብርሃን ነው የምናየው? ብለው ፈርተው ሊሸሹ ሲሉ የእግዚአብሔር መልአክ “አይዟችሁ ልጆች፥እነሆ ለህዝብ ሁሉ የሚሆን ታላቅ ደስታ የምስራች እነግራችኋለሁና አትፍሩ።ይህም ምልክት ይሆንላችኋል።ህፃን በጨርቅ ተጠቅልሎ ተኝቶ ታገኛላችሁ።” አላቸው። ብዙ የሰማይ ሰራዊትከመለኩ ጋር ነበሩ። እግዚአብሔርንም እያመሰገኑ “ክብር ለእግዚአብሔር በአርያም ይሁን ሰላምም በምድር ለሰውም በጎ ፍቃድ።” አሉ። ልጆች ይገርማችኋል የዚያን እለት አበባዎች በደስታ አበቡ።እፅዋት ለመለሙ።ንቦችም ማራቸውን ሰጡ። የቤተልሕውም እንስሳት እኛስ ምን እንስጥ እያሉ ግራ ገባቸው። በመጨረሻ አህያ ከሁሉም የበለጠ አሳብ አመጣች። “ጌታችን የተወለደው በበረት ነው አይደል?” ስትል ጠየቀቻቸው። “አዎን” አሏት። “ታዲያ እኮ ልብስ የለውም።ደግሞም እንደምታዩት ጊዜው ብርድ የበዛበት ነው።” አለች። “እና አህያ ምናችን ልብስ ይሆነዋል ብለሽ አሰብሽ?” አሏት “ለምን ትንፋሻችንን አንሰጥም?”አለች። ሁሉም በጣም ደስ አላቸው።እንስሳቱ ትንፋሻቸውን ሊያበረክቱለት ጌታችን ወደተወለደበት በረት እየሮጡ ሄዱ። ልጆች እናንተም ደስ ካላቸው ጋር አብራችሁ ደስተኞች እንድትሆኑ ባላችሁ ነገር ሁሉ
ስስታም አትሁኑ። እሺ ልጆች።


++++++
ምንጭ፥ ጥበበኛው ሕፃን
የሸዋ ወርቅ ወልደ ገብርኤል