«የአክለክሙ መዋእል ዘሃለፈ ፥ ያለፈው ዘመን ይብቃችኋል» ቅዱስ ያሬድ እና ፩ኛ ጴጥሮስ ፬ ፥ ፫- ፬
በመጋቢ ሀዲስ ምስጢረ ስላሴ ማናየ
ጳጉሜን ፭ ቀን ፳፻፮ ዓ.ም.
«የአክለክሙ መዋእል ዘሃለፈ ፥ ያለፈው ዘመን ይብቃችኋል» ቅዱስ ያሬድ እና ፩ኛ ጴጥሮስ ፬ ፥ ፫- ፬
በቅድሚያ ከዘመነ ማርቆስ ወደ ዘመነ ሉቃስ ያሸጋገረን፤ በመግቦቱ ያልተለየን፤ በችርነቱ የጠበቀን፤ በምህረት አይኖቹ የተመለከተን፤ በብርቱ ክንዶችሁ የደገፈን፤ የዘመናት ባለቤት የፈጥረታት ሁሉ ፈጣሪ ለዚህ ኣመት ስላደረሰን ክብርና ምስጋና ይድረሰው አሜን።
በቸር አድረን የምንውለው፤ ተኝተን የምንነሳው፤ ሰርተን የምናገኘው፤ ደክመን የምንበረታው፤ ታመን የምንደነው፤ ወድቀን የምንነሳው፤ ከቸርነቱ ከጠባቂነቱ የተነሳ ነው። እግዚአብሔር አምላካችን ሰውን ከድንጋይ እና ከእንጨት ለይቶ በደማዊት ነፍስ ከእንስሳት እና ከአራዊት ለይቶ በህያው ነፍስ አክብሯታል በአርያው እና በአምሳሉም ፈጥሯታል። «ወገብሮ እግዚአብሔር ለእጓለ እመህያው እመሬተ ምድር በአሪያሁ ወበአምሳሊሁ ፤ እግዚብሔር አምላክ ሰውን ከምድር አፈር አበጀው በአርያውና በአምሳሉም ፈጠረው» ዘፍ ፩፥፪፮


ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሰማየ ሰማያት ወርዶ ከድንግል ማርያም ከሥጋዋ ሥጋ ከነፍሷ ነፍስ ነስቶ በከብቶች በረት ከተወለደበት ሰዓት ጀምሮ ለሰው ልጅ ድህነት ሲል ጽኑ መከራና ስቃይን ተቀብሏል። በተለይ በመጨረሻው ሰዓት ከሰው ልጅ አዕምሮ በላይ የሆነ ስቃይ፣ መከራ፣ እንግልትና ግርፋትን ተቀብሎ፤ በጲላጦስ ካለበደሉ ከወንበዴዎች ጋር ተፈርዶበት፤ በቀራንዮ አደባባይ በዕለተ አርብ በመስቀል ላይ ተሰቅሎ፤ ነፍሱን በፈቃዱ ሰጥቶ አዳምንና ዘሩን ከሞት ወደ ሕይወት፣ ከጨለማ ወደ ብርሃን መልሶ በሦስተኛው ቀን መቃብር ክፈቱልኝ፣ መግነዝ ፍቱልኝ ሳይል ብርሃንን ተጎናጽፎ በታላቅ ኃይልና ስልጣን በክብር ተነስቷል።