ዜና

በአውሮፓ ተወልደው ላደጉ የአብነት ተማሪዎች ሢመተ ዲቁና ተሰጠ

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በስዊድንና ስካንዴኒቪያን ሀገረ ስብከት የኦስሎ መካነ ቅዱሳን ቅዱስ ገብርኤል ወአቡነ ተክለሃይማኖት ቤተክርስቲያን በአውሮፓ ተወልደው ላደጉ ሰባት የአብነት ተማሪዎች ዲቁና ተሰጠ። 

ለ 4 ዓመታት የአብነት ትምህርታቸውን ሲከተታሉ ለነበሩት ሰባት አዳጊ የአብነት ተማሪዎች ኅዳር 28 ቀን 2012 ዓ.ም. በሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ በብጹዕ አቡነ ኤልያስ ማዕርገ ዲቁና ተሰጥቷል፡፡ 

የኢጣሊያና አካባቢው ሀገረ ስብከት ሊቀጳጳስ ብጹዕ አቡነ ሕርያቆስም እ.ኤ.አ ከ2015 ዓ.ም. ጀምሮ በደብሩ የአብነት ትምህርት ቤትን በማቋቋም፣ የአብነት ትምህርቱንም በማስተማር፤ ተተኪው ትውልድ በትክክል እንዲቀረጽ እና የነገዋ ቤተ ክርስቲያን ተረካቢ እንዲሆን፣ በደብሩ የሚገኙት አዳጊ ወጣቶችም በፈሪሃ እግዚአብሔር፣ በፍቅረ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እንዲያድጉና ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን በሚገባ እንዲያውቋት በማድረግ ረገድ፡ በአጥቢያው የሚገኙትን ማኅበረ ምእመናን በማስተባበር አባታዊ ሓላፊነታቸውን በመወጣት ላይ እንደሚገኙ ተገልጿል፡፡ 

በአሁኑ ጊዜ በደብሩ ከአንድ መቶ በላይ ተማሪዎች የአብነት ትምህርት በመከታተል ላይ የሚገኙ ሲሆን፤ ከእነዚህም ውስጥ ሕጻናት እና ወጣት ሴቶችን ለማበረታታት መዝሙረ ዳዊት ላይ የደረሱ እንዲሁም ውዳሴ ማርያም በመጨረስ ላይ ያሉ ሁለት ሴት ተማሪዎች በብጹዕ አቡነ ሕርያቆስ የተዘጋጀላቸውን የማበረታቻ ሥጦታ ከብጹዕ አቡነ ኤልያስ እጅ ተቀብለዋል። በተጨማሪም በዲቁና ሲያገለግሉ የነበሩ አንድ አገልጋይም በዕለቱ ማዕርገ ቅስና ተቀብለዋል፡፡

በማኅበረ ቅዱሳን አውሮፓ ማእከል የኖርዌይ ንዑስ ማእከል አባላትም የአብነት ትምህርቱ እንዲጠናከር በማስተማር እና በማስተባበር የበኩላቸውን አስተዋጾ በማበርከት ላይ እንደሚገኙ ተገልጿል፡፡

በፍራንክፈርት ከተማ ዐውደ ርእይ ተካሄደ

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን በአውሮፓ ማእከል የጀርመን ንኡስ ማእከል አዘጋጅነት “ኦርቶዶክሳዊት ተዋህዶ ቤተክርስቲያንን አስተምህሮዋን እንጠንቅቅ፤ ድርሻችንን እንወቅ” በሚል መሪ ቃል ኅዳር 28 ቀን 2012 ዓ.ም. በፍራንክፈርት ምስካየ ኅዙናን መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን ዐውደ ርእይ ተካሄደ::

ዐውደ ርእዩን የጀርመን እና አካባቢው ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅና የደብሩ አስተዳዳሪ መልአከ መዊዕ ልሳነ ወርቅ ውቤ በጸሎት የከፈቱት ሲሆን፤ የደብሩ ካህናት እና ከ100 በላይ ምዕመናን ተመልክተውታል። ዐውደ ርእዩ በዋናነትም በአራት ክፍሎች ተደራጅቶ፤ ስለ ቤተ ክርስቲያናችን መሠረተ እምነት፣ ስለ ሐዋርያዊ አገልግሎት ምንነትና እና የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን የሐዋርያዊ አገልግሎት ጉዞ፣ በዓለምና በኢትዮጵያ በተለያዩ ክፍላተ ዘመን ስለነበረው የቤተ ክርስቲያን ተጋድሎ፣ እና ወቅታዊው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ተጋድሎ (በተለይም ከአክራሪዎች እና ከፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ ጋር ያለው ተጋድሎ) በድምጽ ወምስል የታገዘ ገለጻ በዝርዝር ቀርቧል፡፡

በመጨረሻም ማኅበረ ቅዱሳን ባለፉት ዓመታት ውስጥ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን የነበረውን የአግልግሎት ሱታፌ እና አስተዋጽኦ በተንቀሳቃሽ ምስል በታገዘ መልኩ የቀረበ ሲሆን የማኅበረ ቅዱሳን አመሠራረት፣ ርእይ፣ እና የአገልግሎት መስኮች እንዲሁም በአውሮፓ ማዕከል እና በጀርመን ንዑስ ማዕከል ስላለው እንቅስቃሴ በሊቀ ትጉኃን ቀሲስ አብርሃም አሰፋ ሰፊ ገለጻ ተደርጓል፡፡ 

ዐውደ ርእዩን ከተመለከቱ ካህናት እና ምዕመናን ጋር ስለ ወቅታዊ የቤተ ክርስቲያን ፈተናዎች በተለይም እየከፋ ስለሄደው የአብያተ ክርስቲያናት መቃጠል፣ የምዕመናን መገደል እና መፈናቀል ሰፊ ውይይት ተደርጓል፡፡ በውይይቱ ላይ ለተነሱ ጥያቄዎችም በሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ በመልአከ መዊዕ ቀሲስ ልሳነ ወርቅ ውቤ ማብራሪያ ተሰጥቷል። 

የጀርመን ንዑስ ማዕከልም ለዝግጅቱ መሳካት ከጅማሬ እስከ ፍጻሜ ከፍተኛ ትብብር ያደረጉትን የደብሩን አስተዳዳሪ እና ሰበካ ጉባኤ፣ ዐውደ ርእዩ ላይ በገላጭነት የተሳተፉትን የደብሩን ሰንበት ትምህርት ቤት አባላት፣ ለዝግጅቱ መሳካት በተለያየ መልኩ እገዛ ያደረጉትን እንዲሁም ረጅም ሰዓት ወስደው ዐውደ ርእዩን የጎብኙትን ምዕመናን በሙሉ አመስግኖ ይህ ቀና ትብብር ለወደፊትም እንደማይለየው ያለውን ጽኑ እምነት ገልጿል። 

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መዋቅራዊ አንድነቷን መመለስ ተከትሎ፣ ማኅበረ ቅዱሳን በነበረው የአስተዳደር ልዩነት ምክንያት አገልግሎቱን ሳይሰጥ በቆየባቸው አጥቢያዎች አገልግሎቱን ተደራሽ ለማድረግ በመንቀሳቀስ ላይ እንደሚገኝ የማኅበረ ቅዱሳን ተወካይ መልአከ ሣህል ቀሲስ ያብባል ሙሉዓለም ገልጸዋል። ይህ ዐውደ ርእይም ማኅበረ ቅዱሳን ብዙ ካህናት እና ምዕመናን ባሉት፣ የራሱ ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን ባለቤት በሆነው፣ እንዲሁም ከሕጻናት እስከ አዋቂዎች ሰፊ አገልግሎት በሚሰጥበት በፍራንክፈርት ምስካየ ኅዙናን መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን ያካሄደው የመጀመሪያ አገልግሎቱ ነው፡፡

በመጨረሻም መልአከ መዊዕ ቀሲስ ልሳነ ወርቅ ውቤ ዐውደ ርእዩ እንዲሳካ ድጋፍ ያደረጉትን ሁሉ አመስግነው ከምንጊዜውም በላይ ለቤተክርስቲያን ኅልውና በጋራ የምንቆምበት ጊዜ በመሆኑ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ለመደገፍ ሁላችንም የበኩላችንን አስተዋጽዖ ልናደርግ እንደሚገባ በማሳሰብ መርሐ ግብሩን በጸሎት ዘግተዋል፡፡


በቅድስት ቤተ ክርስቲያን እየደረሰ ያለውን ጥቃት በመቃወም በተለያዩ የአውሮፓ አገራት ሰላማዊ ሰልፍ ተደረገ፡፡

መንግሥት የዜጎችን ደኅንነት የማስጠበቅ ግዴታ ያለበት በመሆኑ በአገር ቤት በምትገኘው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን እና በልጆቿ ላይ እየደረሰ ያለውን ጥቃት የኢትዮጵያ መንግሥት እንዲያስቆም፣ አብያተ ክርስቲያነቱን ያቃጠሉ በልጆቿ ላይም ግፍን ያደረጉ ሰዎችን ለፍርድ እንዲያቀርብ ለመጠየቅ በአውሮፓ በሚገኙ ሦስቱ አህጉረ ስብከት (የስዊድንና የስካንዴኒቪያን ሀገረ ስብከት ፣ ጀርመንና አካባቢው ሀገረ ስብከት እና የጣልያንና አካባቢው ሀገረ ስብከት) አስተባባሪነት በተለያዩ የአውሮፓ ከተሞች ሰላማዊ ሰልፍ  ተካሂዷል፡፡

ሰላማዊ ሰልፎቹ በ ጣልያን ሮም፣ ቤልጅየም ብራስልስ፣ ጀርመን በርሊን፣ ሆላንድ ዘሄግ፣ ስዊዘርላንድ ጄኔቫ.፣ ስዊድን ስቶክሆልም እና በ ኦስትሪያ ቪዬና ኅዳር 26 ቀን 2012 ዓ.ም. ተካሄደዋል፡፡ በተጨማሪም በፈረንሳይ ፓሪስ ኅዳር 25 ቀን 2012 ዓ.ም. ተካሂዷል፡፡ በሰልፎቹም ላይ የጀርመን እና አካባቢው አገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብጹዕ አቡነ ዲዮናስዮስ፣ የሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ፣ የየአድባራት አስተዳዳሪዎችና አገልጋይ ካህናት፣ የሰ/ት/ቤት ወጣቶች እና ምእመናን ተገኝተዋል፡፡ በተመሳሳይ መልኩ በሌሎቹም አገራት የየአህጉረ ስብከት ተወካዮች፣ የየአድባራት አስተዳዳሪዎች፣ ካህናት፣ የሰ/ት/ቤት ወጣቶች እና ምእመናን በተገኙበት በታላቅ ድምቀት ተከናውኗል፡፡

ሰልፉ በሁሉም ሥፍራ በጸሎተ ወንጌል የተጀመረ ሲሆን፡ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን እየደረሰ ያለው መገፋትን እግዚአብሔር እንዲመለከትም ጸሎተ ምሕላ ደርሷል፡፡ በሰልፉ ላይ የተገኙት አባቶችም “ጩኸታችንን ለዓለም ሕዝብ በማሰማት ብቻ እንዳይገታ ይልቁንም ከፊት ይልቅ ይበልጥ ወደ እግዚአብሔር በመቅረብ ስለ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን እና እግዚአብሔርን ስለ ምትወድደው አገራችን በፍጹም ኀዘን ልናሳስብ ይገባል” በማለት መልእክት አስተላልፈዋል፡፡ ሰላማዊ ሰልፎቹ የተካሄዱበት ዓላማም በቤተ ክርስቲያን ላይ እየደረሰ ያለውን ግፍና መከራ ለማውገዝ፣ እንዲቆም ለመጠየቅ፣ ኢትዮጵያ ውስጥ የሚገኙ ሚዲያዎች ተገቢውን ሽፋን ሊሰጡት ስላልቻሉ የተለያዩ ሚዲያዎች እና የዓለሙ ማኅበረሰብ እንዲያውቀው እና ይህን ችግር እየፈጠሩ ያሉ አካላት ላይም ሆነ የኢትዮጵያ መንግሥት ላይ ጫና እንዲፈጥሩ ለማድረግ መሆኑን በሰልፉ ላይ የተገኙ አባቶችና አስተባባሪዎች ተናግረዋል፡፡

 በክርስቲያኖች ላይ የተቃጣውን ጥቃት የዓለሙ ማኅበረሰብ እንዲያውቀውና እንዲያወግዘው ለማድረግ ታስቦ የተደረገው ሰልፍ፡ በየአህጉረ ስብከቶቹ ሊቃነ ጳጳሳት በየሀገራቱ ቋንቋዎች የተጻፉት የአቤቱታ ደብዳቤዎች በሮማ ለፓርላማው ጽ/ቤት፣ በበርሊን ለጀርመን ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የአፍሪካ ዴስክ፣ በጀርመን ለአውሮፓ ህብረት ጽ/ቤት፣ ለፈረንሳይ እና አሜሪካ ኢምባሲዎች፣ በዘሄግ ለኢትዮጵያ ኤምባሲ፣ በስቶክሆልም ለስዊድን ገዢ ፓርቲ፣ በጽሑፍ ቀርበዋል፡፡ አባቶችና የምእመናን ተወካዮችም ጉዳዩ ከሚመለከታቸው የየሀገራቱ ተዋካዮች ጋር በመነጋገር ለተጨማሪ ውይይት ቀጠሮ ማስያዛቸው ታውቋል፡፡ በሆላንድም እንዲሁ የኢትዮጵያው አምባሰደር የሰልፉን ተወካዮች በቢሮአቸው በመቀበል አነጋግረዋቸዋል፡፡

በሰላማዊ ሰልፉ ላይ ከተላለፉት መልእክታት እና መፈክሮች መካከል ሀገር ከነድንበሩ፣ ነጻነትን ከነክብሩ፣ ፊደልን ከነቁጥሩ ያስረከበች ቅድስት ቤተክርስቲያን ይህ አይገባትም፤ የቤተ ክርስቲያን ጩኸትና አቤቱታ ይሰማ፤ አክራሪ ብሔርተኞችና ጽንፈኞች እጃቸውን ከቤተክርስቲያን ላይ ያንሡ፤ ቤተክርስቲያንን ያቃጠሉ፣ ካህናትንና ምዕመናንን የገደሉ በሕግ ይጠየቁልን፤ የሚሉ እና ሌሎችም ይገኙበታል፡፡

ሰልፉ ፍጹም ሰላማዊ በሆነ መንገድ በተያዘላቸው መርሐ ግብራት መሠረት የተከናወኑ ሲሆን፤ በሥራ ቀን የተደረገ ቢሆንም የተገኙት የምእመናን ቁጥር ከፍተኛ መሆኑ ተገልጿል፡፡

በሮም የተካሄደው ሰላማዊ ሰልፍ ለሁለተኛ ጊዜ መሆኑና የ የታላቋ ብሪታንያ እና አየርላንድ ሀገረ ስብከትም ከወራት በፊት በተመሳሳይ መልኩ በለንደን ከተማ ሰላማዊ ሰልፍ ማድረጉና በለንደን ከኢትዮጵያ ኢምባሲ ጋርም ውይይት ማካሄዱ ይታወሳል፡፡

ከየከተማዎቹ የተወጣጡ የተወሰኑ ፎቶዎች

ሮም ፤ ጣልያን
ጀርመን ፤ በርሊን
ስዊድን ፤ ስቶክሆልም
ሆላንድ ዘሄግ በ ኢትዮጵያ ኤምባሲ ውስጥ

፮ተኛው ሐዊረ ህይወት በጀርመን ሀገር ሆክስተር ከተማ ተካሄደ።

ሚያዚያ 17 ቀን 2011 ዓ.ም

በጀርመን ንዑስ ማዕከል

በኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ/ሰ/ት/ቤ/ማ/መ/ ማኅበረ ቅዱሳን አውሮፓ ማዕከል የጀርመን ንዑስ ማዕከል ያዘጋጀው፥ ፮ተኛው ሐዊረ ህይወት በጀርመን -ከሃኖቨር  ከተማ 90 ኪሜ ርቀት ላይ በምትገኘው ሆክስተር ከተማ በሚገኘው የግብጽ ኦርቶዶክስ ቅድስት ማርያም እና ቅዱስ ማውሪስ ገዳም ከሚያዚያ ፬ እስከ ፮ ድረስ በተሳካ ሁኔታ ተካሄደ።

ዓርብ ማምሻውን አባቶች ካህናት በተገኙበት በጸሎት ተከፍቶ፥ ሊቀ ትጉኃን ቀሲስ አብርሃም እንኳን ደህና መጣችሁ ንግግር አሰተላልፈዋል። በመቀጥልም ቀሲስ ግሩም ታየ የዕለቱን ትምህርት ካስተማሩ በኋላ፥ የእራት መስተንግዶ ተካሂዶ የምሽቱ መርሐ ግብር ተጠናቋል።

ቅዳሜ ጠዋት በቤተክርስቲያናችን ካህናትና ዲያቆናት ሥርዓተ ቅዳሴ የተፈጸመ ሲሆን፥ ከቅዳሴ በኋላ በነበረው የጠዋቱ መርሐግብር መክፈቻ ላይ የገዳሙ የበላይ ጠባቂ እና በግብጽ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን የሰሜን ጀርመን ሊቀ ጳጳስ ብጹዕ አቡነ ደሚያን “እንኳን ወደ ገዳማችሁ በደህና መጣችሁ፤ በመምጣታችሁ ተደስቻለሁ በርቱ ጠንክሩ በነፍስም በሥጋም ጎልምሱ” በማለት መልእክት አስተላልፈዋል።

 

ለጉባዔው ከተዘጋጁት ዋና ትምህርቶች መካከል፥ “ነገረ እግዚአብሔር” በሚል ርዕስ በመጋቤ ምሥጢር ዶ/ር ኅሩይ ኤርምያስ ተሰጥቷል። መምህሩ ሀልዎተ እግዚአብሔርን በሚመለከት የቤተክርስቲያንን አስተምህሮ፥ ከተለያዩ የፍልስፍና አስተምህሮዎች አንጻር በግልጽ አቀራረብ ያስተማሩ ሲሆን፥ በተጨማሪምየእግዚአብሔር ስሞችንና ባህርያት በሰፊው የዳሰሰና፥ ለተሳታፊዎች ብዙ ዕውቀትን ያስጨበጠ ትምህርት ነበር። 

በመቀጠልም መልአከ ስብሐት ተክሌ ሲራክ ከትምህርቱ ርዕስ ጋር የሚሄድ ያሬዳዊ ዜማ “አነ ቀዳማዊ ወአነ ደኃራዊ ይስማ ሰማይ ወታጽምእ ምድር” ትርጉሙም “መጀመሪያ እኔ ነኝ፥ መጨረሻም እኔ ነኝ ፤ ሰማይ ይስማ ምድርም ታድምጥ” ካቀረቡ በኋላ፥ ሊቃውንት ለሚያዚያ 5 አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ በዓል ያዘጋጁትን የማኅሌት ዜማ አሰምተዋል።

የጀርመንና አካባቢው ሀገረ ስብከት ዋና ጸሐፊ ቆሞስ አባ ስብሐት ለአብ ሀገረ ስብከቱን ወክለው ባስተላለፉት መልእክት፥ ማኅበሩ እየሠራው ያለውን አገልግሎት አድንቀው፥ ሀገረ ስብከቱ እንደቀድሞው ማኅበሩ ቤተክርስቲያንን ለመደገፍ የሚያደርገውን እንቅስቃሴ በቅርበት ለመክታተል እና እገዛ ለማድረግ፥ እንዲሁም ማኅበሩ አገልግሎቱን ከሌሎች የሀገረ ስብከቱ ክፍሎች ጋር በቅንጅት እንዲያደርገው ፍላጎቱ እንደሆነ ገልጸዋል።

በመቀጠልም ከምዕመናን ለቀረቡ መንፈሳዊ ጥያቄዎች በሊቃውንተ ቤተክርስቲያን መልስ ከተሰጠ በኋላ፥ በንዑስ ማዕከሉ ሚድያ ክፍል የማኅበረ ቅዱሳን ሚዲያ እንቅስቃሴ ዓላማ፥ ያለበት ደረጃ፥ ያሉት ተግዳሮቶች፥ የሚዲያ ሽፋኑ ከሌሎች አብያተ ክርስቲያናት ጋር በንጽጽር የቀረበ ሲሆን፥ ከምዕመናን ምን አንደሚጠበቅም ጥናቱ ጠቁሟል።

በማስከተልም ለጉባዔው የተዘጋጀውን ትምህርት “ምሥጢረ ንስሐ” በሚል ርዕስ የሰጡት ቀሲስ ዶ/ር ያብባል ሙሉዓለም ናቸው። መምህሩ በተለይም በተሠራ ኃጢአት ከመጸጸት እና ከመመለስ በተጨማሪ ለካህን መናዘዝ የምሥጢረ ንስሐ ዋነኛው አካል መሆኑን ከመጽሐፍ ቅዱስ እና ከሥርዓተ ቤተክርስቲያን እየጠቀሱ በሚገባ ያስረዱ ሲሆን፥ በተጨማሪም የቅዱሳንን የንስሐ ሕይወት አሁን እኛ ከምንኖረው ሕይወት ጋር በማዛመድ ዘመኑን የዋጀ ትምህርት ሰጥተዋል።

ሌላው በሐዊረ ህይወቱ ትኩረት የተሰጠው፥ በማኅበረ ቅዱሳን እየተካሄደ ያለውን የስብከተ ወንጌል ማስፋፊያ ፕሮጀክቶችና ተግዳሮቶች፥ እንዲሁም የምዕመናንና ማኅበራት ሚና ምን መምሰል እንዳለበት በዲ/ን ዶ/ር መርሻ አለኸኝ ከቀረበ በሁዋላ ብዙሃንን በእንባ ያራጨው ከጉዳዩ ጋር ተያያዝነት ያለው የታየው ቪዲዮ ነው። ይህንንም ያዩ ካህናትና ምዕመናን እስካሁን ይህንን ነገር በደንብ ሳይገነዘቡ መቆየታቸው ምን ያህል እንደቆጫቸው ተናግረው፤ ከዚህ ቀን ጀምሮ ለታቀዱት ፕሮጀክቶች የተቻላቸውን እንደሚያበረክቱም ቃል ገብተዋል።

የቅዳሜ ፍጻሜ መርሐግብር የነበረው የገዳሙን ሙዚየም መጎብኘት ነው። ጉብኝቱም ታዳሚዎችን ያስተማረ ብቻ ሳይሆን በመንፈሳዊ ቅናት እንዲቃጠሉ ያደረገም ነበር።  ከዚህም መካከል በጀርመን የሚኖሩ ግብጻውያን ቁጥራቸው ከኢትዮጵያውያን የሚያንስ ሲሆን፥ ነገር ግን በጀርመን ሀገር ሁለት ትልልቅ ገዳማትን እና ሌሎች ተቋማትን መግዛት የቻሉበት ትጋት እና አርቆ አሳቢነት፥ እንዲሁም ገዳሙ ውስጥ የግብጽን ቤተክርስቲያን ታሪክ እና አስተምህሮ ለማስተዋወቅ በጀርመንኛ ቋንቋ ያዘጋጁት ቋሚ ዐውደ ርዕይ ወዘተ ተጠቃሽ ናቸው።    

በመጨረሻም እሁድ ጠዋት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያንና የግብጽ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ካህናትና ዲያቆናት በጋራ ሥርዓተ ቅዳሴ አካሂደው የ፮ተኛው ሐዊረ ህይወት መርሐ ግብር ፍጻሜ ሆኖዋል።

በመንፈሳዊ ጉባዔው ላይ ወደ 150 የሚጠጉ ምዕመናንና ህጻናት የተገኙ ሲሆን ከግማሽ በላይ የሚሆኑት ሐዊረ ህይወት መርሐ ግብር ላይ ሲገኙ ለመጀመሪያ ጊዜ እንደሆነና በነበረው ጉባዔ እጅግ እንደተደሰቱ፥ ብዙ መንፈሳዊ ትምህርቶችንና በቤተክርስቲያን እየተካሄዱ ስላሉ አገልግሎቶች ዕውቀት እንዳገኙ ተናግረዋል።

        

የጀርመን ንዑስ ማዕከል ከዚህ በፊት 5 ሐውረ ሕይወቶችን ፍራንክፈርት አካባቢ በሚገኘው ክሩፈልባህ ከተማ ባለው የቅዱስ እንጦን ገዳም ማድረጉ የሚታወስ ነው።

የሆላንድ ንዑስ ማዕከል ዓውደ ርዕይ አካሄደ

ሚያዚያ 07 ቀን 2011 ዓ.ም

በሆላንድ ንዑስ ማዕከል

በሆላንድ አምስፎርት ከተማ “ኦርቶዶክሳዊት ተዋህዶ ቤተክርስቲያንን አስተምሮዋን እንጠንቅቅ፣ ድርሻችንን እንወቅ” በሚል ርዕስ ዓውደ ርዕይ ተካሄደ፡፡በሐመረ ኖህ ቅድስት ማርያም ቤተክርስቲያን ውስጥ ቅዳሜ ፳፩ / ፪ሺ፲፩ ዓም የተደረገው ይህ ዐውደ ርእይ ቀድሞ ከተካሄደው አውደ ርእይ ከረጅም ጊዜ በኋላ ቆይቶ የተካሄደ መሆኑን የቆዩ የንዑስ ማዕከሉ አባላት ይናገራሉ። በአራት ክፍል የተዘጋጀው ይህ ዓውደ ርዕይ በምስል ወድምጽ በተደገፈ ገለጻ ቀርቧል።ቤተክርስቲያን ማናት እና አስተምሮዋ በክፍል አንድ ሲቀርብ፤ ሐዋርያዊው ተልእኮ እንዲሁም በተልእኮው  የገጠሙ ተግዳሮቶችና የተደረጉ ተጋድሎዎች በክፍል ሁለትና ሶስት በቅደም ተከተል ቀርበው፤ በመጨረሻም በክፍል አራት የምዕመናን ድርሻ ምን ሊሆን እንደሚችልም ያመላከተም ነበር።

Image may contain: one or more people, people standing and wedding Image may contain: 1 person, indoor

በአውደ ርእዩ የተሳተፉ ምዕመናንም እንዲህ አይነት ዝግጅት በየዓመቱ ቢደረግ፤ እኛ ያየነውን በሌሎች አጥቢያዎች ያሉ ምዕመናንም እንዲያዩት ቢደረግ በሕብረት ወደ መስራት ያመጣን ይሆናል በማለት አስተያየት ሰጥተዋል፡፡ በተለይ ትዕይንት ክፍል ሶስትና አራት የቀደሙ አባቶቻችንና እናቶቻችን ይህችን ቤተክርስቲያን እንዴት እንዳቆዩልንና ዛሬስ ምን እያደረግን እንደሆነ የሚያነጻጽር በመሆኑ፤  ወደ ራሳችን ተመልሰን እራሳችንን እንድመለከት አድርጎናል ብለዋል።

ትዕይንቱን መርቀው የከፈቱት የደብሩ አስተዳዳሪ አባ ኃይለማርያምም ማኅበሩ ለቤተክርስቲያን ፈርጥ መሆኑን እናውቃለን ግን በሆላንድ ያለው እንቅስቃሴ እኔ በማውቀው ውስን ነው፡አሁን ያየነው መርሐ ግብር በራሱ ትልቅ ለውጥ መሆኑን መመልከት ችያለሁ። ከዚህ ቦኃላም ማኅበሩ ከቤተክርስቲያን የተረከበውን የልጅነት አደራ እንደሚወጣ እገምታለው  ብለዋል፡፡ አያይዘውም ተጀምሮ እስኪያልቅ ምዕመኑ ሳይሰለች እንዲቆይ ያደረገበት የጊዜ አጠቃቀምና አቀራረብ ዘዴ የማኅበሩን ማንነት ያሳየበት ነው ብለው ከ አውደ ርዕዩ ቦኃላ አስተያየታቸውን ገልፀዋል፡፡ የሰበካ ጉባኤው አባላትም በመርሐግብሩ ተደስተው ሌሎች መርሐ ግብራትንም ማኅበሩ በአጥብያቸው እንደሚያደርግ እና ለዚህም የሰበካ ጉባዔው እና ምእመናንም በማንኛዉም ነገር ለመተባበር ፈቃደኛ መሆናቸውን ገልፀዋል።

Image may contain: one or more people and indoor

የሆላንድ ንዑስ ማዕከል በአውሮጳ ማዕከል ስር ካሉት ንዑስ ማዕከላት አንዱ መሆኑም ይታወቃል፡፡

ወስብሃት ለእግዚአብሔር         

የጀርመን ንዑስ ማዕከል ሦስተኛውን ዐውደ ርዕይ በሙኒክ ከተማ አካሄደ።

ሚያዚያ 02 ቀን 2011 ዓ.ም

በጀርመን ንዑስ ማዕከል

“ቤተ ክርስቲያናችንን እንወቅ አስተምህሮዋን እንጠንቅቅ” በሚል መሪ ቃል፥ የተዘጋጀው ዐውደ ርእይ በተለያዩ የዓለማችን ክፍሎች ለሚገኙ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን በማኅበሩ ንዑሳን ማዕከላት አስተባባሪነት እየቀረበ የሚገኝ ሲኾን፥ ዋና ዓላማውም ቤተክርስቲያንን ለምዕመናን በማስተዋወቅ አስተምህሮዋንና ኹሉን ዓቀፍ ህልውናዋን ለማስቀጠል የበኩሉን አስተዋጽዖ ለማድረግ ነው።

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮና ማንነት፤ ሐዋርያዊ አገልግሎቷንና በዘመናት የገጠማትን ተጋድሎ፥ እንዲኹም በአሁኑ ወቅት አንዳንድ ያሉባትን ውስንነቶች ጭምር የሚያስረዳው ዐውደ ርዕይ በጀርመን ቫርያ ግዛት ዋና ማዕከል በኾነችው በሙኒክ ከተማ በደብረ ብስራት ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን ለኢትዮጵያውያንንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን መጋቢት ፳፩ እና ፳፪፥፪፻፲፩ ዓ/ም በጥሩ ሁኔታ ቀርቧል።

ዐውደ ርዕዩ በብፁዕ አቡነ ናትናኤል የምሥራቅ ወለጋ ቄለም ወለጋና ሆሮ ጉድሩ አህጉረ ስብከት ጳጳስ ቃለ ምዕዳን ተባርኮ የተከፈተ ሲኾን፥ በአካባቢው የሚገኙ የአብያተ ክርስቲያናት አስተዳዳሪዎችና አገልጋዮችም በመክፈቻው ላይ ተገኝተዋል። ብፁዕ አቡነ ናትናኤል ከመክፈቻ ፕሮግራሙ ባስተላለፉት አባታዊ መልእክት እንዲህ ዓይነቱ ዝግጅት በሰማያት ያለውን እግዚአብሔርን የሚገልጥ፥ በሰዎች ፊት የሚበራ መልካም ሥራ ስለኾነ ሊቀጥልና ሊበረታታ እንደሚገባው አስገንዝበዋል። ብፁዕነታቸው አክለውም እነዚህ መንፈሳዊ ጉባዔያት ሰውን ወይም ማኅበራትን ለማክበርና ስምን ለማስጠራት ታስበው የሚደረጉ ሳይኾኑ፥ እግዚአብሔር እንዲመሰገንና ህዝበ ክርስቲያኑ በአምልኮ ጸንቶ መንግስቱን እንዲወርስ የሚያስችሉ ስለኾኑ፥ አሁን ባሉበት ኹነት የእግዚአብሔርንና የቤተ ክርስቲያንን ክብር አጉልተው በመግለጥ እንዲቀጥሉ አደራ ብለዋል።

 

ዐውደ ርዕይውን የተከታተሉት ብዙዎች ምዕመናን በበኩላቸው በዚህ መልኩ የተዘጋጁ መንፈሳዊ ዐውደ ርዕይዎችን ዐይተው እንደማያውቁና በዝግጅቱም ደስተኞች እንደኾኑ ገልጸዋል። ቤተ ክርስቲያናችን ዘመኑን ዋጅታ፥ ትውልዱን ለመጠበቅ እየተጋች መኾኑን የሚያሳይ መልካም ጅምር ነው፥ በማለትም ስለ ዐውደ ርዕይው የነበራቸውን ስሜት አካፍለዋል። ወደፊትም እንዲህ በተደራጀ መልኩ ዝግጅቶች በተደጋጋሚ ቢደረጉ መልካም ነው፥ በማለት አዘጋጁን የጀርመንን ንዑስ ማእከልን አሳስበዋል።

ዐውደ ርዕዩ በኹለት ቀን ዝግጅት በዘጠኝ ዙር ተጎብኝትዋል። ከከተማው ውጭ ያሉ ማኅበራትም ብዙ ኪሎ ሜትሮችን ተጉዘው በመምጣት ተሳታፊዎች ሆነዋል። ዐውደ ርዕዩ በሌሎች አካባቢ እንዲቀርብ በቀረበው ጥያቄ መሠረት ባጭር ጊዜና በተቀናጀ መልኩ በሌሎች የበቫርያ ግዛት በሚገኙ ከተሞች ለማሳየት እቅድ ላይ እንዳለም በንዑስ ማእከሉ ተጠቁማል።

በቦታው ከተዘጋጀው ዐውደ ርዕይ በተጨማሪ በእለተ እሑድ ከቅዳሴ በኋላ ከ350 በላይ ለሚኾኑ የደብሩ ምዕመናን ማኅበረ ቅዱሳን በ2011 ዓ/ም ሊሠራቸው ካቀዳቸው የፕሮጀክት እቅዶች አምስት ያክሉን በመምረጥ ከአጭር ዘጋቢ ፊልም ጋር ገለጻ ተደረጓል። የፕሮጀክት ገለጻው ዓላማ የማኅበሩን እቅንቅስቃሴ በሐሳብ፥ በጉልበትና በገንዘብ ለመደገፍ ፈቃደኛ የኾኑ አቅም ያላቸው አካላት ተሳትፎ እንዲያደርጉ ለማሳወቅ ታስቦ የቀረበ ሲኾን፥ ብዙዎችም በደስታ ተከታትለው፥ ቀና ምላሻቸውንም አሳይተውበታል። በመጨረሻም ዐውደ ርዕዩ እሑድ ከቀኑ 11 ሰዓት ላይ ተጠናቋል።

 

የጣልያን እና አካባቢው ሀገረ ስብከት የምሥረታ ጉባኤውን አካሄደ

ጥር 14 ቀን 2011 ዓ.ም

 

“ስለ ሰላም፣ ስለ እርቅ እና አንድነት ሁላችሁም ትናገራላችሁ፤ እኔም ብመኘውም ብቻዬን ግን አላመጣውም፣ እናንተም እርዱኝ” ብፁዕ አቡነ ሕርያቆስ።

ብፁዕ አቡነ ሕርያቆስ የጣልያንና አካባቢው ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ

በአውሮፓ አኅጉር በአዲስ መልክ ከተዋቀሩት አራት ሀገረ ስብከቶች አንዱ የሆነው የጣልያን እና አካባቢው (ጣልያን፣ ቤልጅዬም፣ ፈረንሳይ፣ ግሪክ እና ቱርክ) ሀገረ ስብከት የመመሥረቻ ጉባኤውን በጣልያን ዋና ከተማ ሮም አካሄደ። ጉባኤው ጥር 3 እና 4 ቀን 2011 ዓ.ም በሀገረ ስብከቱ ጳጳስ በብፁዕ አቡነ ሕርያቆስ ሰብሳቢነት ተካሂዷል። በጉባዔው ላይ በሀገረ ስብከቱ ስር ከሚገኙ አሥራ ስምንት አብያተ ክርስቲያናት ከጣልያን፣ ፈረንሳይ፣ ቤልጅየም፣ ግሪክ እና ከቱርክ የተሰባሰቡ አስተዳዳሪዎች እና የሰበካ መንፈሳዊ አስተዳደር ጉባዔ ተወካዮች ታድመዋል።

ተሳታፊ ካህናት አባቶች እና ተወካዮች የእርስ በርእስ ትውውቅ እና የመጡበትን አጥቢያዎች አጭር የሥራ ሪፖርት ያቀረቡ ሲሆን በሀገረ ስብከቱ በሚገኙት በርካታ አብያተ ክርስቲያናት ከመጠነኛ እስከ ከፍተኛ ደረጃ የደረሱ ችግሮች እና አለመግባባቶችን ያስተናገዱ መሆናቸው ተጠቁሟል። ከእነኚህም በእግዚአብሔር እርዳታ መፍትሔ የተሰጣቸው አጥቢያዎች ሲኖሩ በአሁኑ ወቅት አለመግባባቱ የተባባሰባቸው እንዳሉ ከቀረቡት ሪፖርቶች ለመረዳት ተችሏል። እነኚህን ችግሮች ለመፍታት ሀገረ ስብከቱ እና ሁሉም ባለድርሻ አካላት የበኩላቸውን ጥረት እንዲያደርጉም ጥሪ ቀርቧል።

የሀገረ ስብከቱ ጳጳስ በየአጥቢያው ያሉትን ችግሮች እንዲሁም ሥርዓትን እና ሕገ ቤተክርስቲያንን ያልጠበቀ አሠራር ከሀገረ ስብከታቸው እንዲጠፋ ጥብቅ ማሳሰቢያ ሰጥተዋል። “ስለ ሰላም፣ ስለ እርቅ እና አንድነት ሁላችሁም ትናገራላችሁ፣ እኔም ብመኘውም ብቻዬን አላመጣውም፣ አናንተም እርዱኝ” በማለት ሰላምን ለማስፈን እንዲቻል የጉባኤተኛውን ቀና ትብብር የጠየቁት ብፁዕ አቡነ ሕርያቆስ፣ “ለዓለም ሰላምን የምትሰብክ ቤተክርስቲያ ውስጥ ሆነን፣ የእኛን ችግር ራሳችን መፍታት አቅቶን፣ ገመናችንን ወደ ዓለማዊ ፍርድ ቤት እና ዳኛ በመውሰድ ከፍተኛ የገንዘብ እና የጉልበት ኪሳራ ላይ ወድቀናል፣ ይህ ገንዘብ ለገዳማት እና አብነት ትምህርት ቤቶች ማበልጸጊያ ይውል ነበር።” ሲሉ ቁጭታቸውን ገልጸዋል።

በአዲስ የተዋቀረው የሀገረ ስብከቱን የተለያዩ ክፍሎች የሚያስተባብሩ እና አገልግሎቱን የሚመሩ ሰባት አባላት ያሉት የአስተዳደር ጉባኤ የተዋቀረ ሲሆን ጉባኤው፣ መልአከ ሕይወት ቀሲስ ፍስሐ ድንበሩን (ከፈረንሳይ) የሀገረ ስብከቱ ዋና ጸሐፊ በማድረግ ሰይሟል። በሌላ በኩል በሕገ ቤተክርስቲያን መሠረት የሀገረ ስብከቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ በጳጳሱ አቅራቢነት ቅዱስ ፓትርያርኩ የሚመድቡ መሆኑ ተገልጿል። ይህ አዲስ የአስተዳደር ጉባኤ በተወከለበት አካባቢ ያለውን የቤተክርስቲያን አገልግሎት ለማሳለጥ በተለይም ከዚህ በፊት ከነበሩት ሙከራዎች በተሻለ መልኩ ዘመኑን የዋጀ፣ ግልጽነት የሰፈነበት፣ እና በጥናት ላይ የተመሠረተ አሠራር እንዲያመጣ ሓላፊነት ተጥሎበታል። ከዚህ ጋር በተያያዘ የሀገረ ስብከቱ መንበረ ጵጵስና በጣልያን ዋና ከተማ በሮም እንዲሆን የተወሰነ ሲሆን አገልግሎቱን በአስተማማኘነት ለማስቀጠል እንዲቻልም ሁሉም አጥቢያዎች እንደየደረጃቸው የገቢ ፈሰስ እንዲያደረጉ ውሳኔ ተላልፏል።

ሀገረ ስብከቱ በዚህ ጉባኤ በጸደቀለት መመሪያ መሠረት፣ ከጥገኝነት ነጻ የሆነ እና የትኛውም ሊቀ ጳጳስ በተዘዋወረ ጊዜ በሻንጣው ይዞት የሚዞር ዕቃ እንዳይሆን፣ ነገር ግን ራሱን የቻለ የገንዘብ እና የቁሳቁስ አቅም፣ የተጠናከረ ቢሮ እና አስተዳደር እንዲኖረው ተሳታፊዎች ጠቁመዋል። ለዚህም እንዲረዳ ከአብያተ ክርስቲያናት ከሚሰበስበው ገቢ በተጨማሪ ልዩ ልዩ የልማት ሥራዎችን በመሥራት ሀገረ ስብከቱን እንዲያጠናክር ለአስተዳደር ጉባኤው ምክር ተችሮታል። በሀገረ ስብከቱ ውስጥ የካህናት እና አገልጋዮች ምደባ እንዲሁም አጠቃላይ አሠራር ወጥነት ባለው መልኩ እና ከጠቅላይ ቤተክህነት ጋር በመናበብ እንዲያከናውንም ጥሪ ቀርቧል።

ለሁለት ቀናት የተደረገው የምስረታ ጉባኤው በሀገረ ስብከቱ ሊሠሩ ይገባቸዋል ያላቸውን የትኩረት አቅጣጫዎች በመጠቆም አዲስ ለተቋቋመው የአስተዳደር ጉባኤ የቤት ሥራ ሰጥቷል። ከነዚህም መካከል በሀገረ ስብከቱ ሰላምን እና አንድነትን ማጠናከር፣ በአብያተ ክርስቲያናት መካከል አንድነትን መፍጠር፣ በጥናት ላይ የተደገፈ አሠራር መዘርጋት፣ በአውሮፓ መልካም አጋጣሚዎችን ማጥናት፣ ስብከተ ወንጌልን ማስፋፋት፣ በጥገኝነት ጠያቂዎች ማቆያ ካምፕ አካባቢ ትምህርት መስጠት፣ የአገልጋዮች ስልጠና ማዕከል መከፈት፣ አጥቢያዎች የራሳቸው የሆነ ሕንጻ ቤተክርስቲያን ማስገኘት፣ እና ሀገረ ስብከቱን ማጠናከር የሚሉት ይገኙበታል።

በጉባኤው መጨረሻ ላይ ታላቅ ሥራን እግዚአብሔር ሠርቷል። ይህም፣ በሮም ደብረ ጽዮን ቅድስት ማርያም እና በደብረ ከነዓን ቅድስት ሥላሴ አብያተ ክርስቲያናት አገልጋዮች መካከል ተፈጥሮ ለዓመታት የቆየው አለመግባባት “ድንጋይ ባገኝ፣ ድንጋይ ተሸክሜ ይቅር ይባባሉ ዘንድ በለመንኳቸው” ሲሉ በተደመጡት የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ በአቡነ ሕርያቆስ ጸሎት እና በተሳታፊዎች አቀራራቢነት በሁለቱ አጥቢያዎች ካህናት እና ተወካዮቻቻው አማካኝነት እርቅ እና ሰላም እንዲወርድ ሆኗል። ይህ እርቅ የምሥረታ ጉባኤው ታላቅ ስኬት ሲሆን በሁለቱ አጥቢያዎች የተጀመረው የእርቅ እና የሰላም ጉዞ በአጠቃላይ በሀገረ ስብከቱ ውስጥ ለሚገኙ አብያተክርስቲያናት አገልግሎት መጠናከር ከፍተኛ አስተዋጾ እንዳለው ተገልጿል። በሌሎች አጥቢያዎች የሚታዪ አለመግባባቶችም በዚህ መልኩ መፈታት እንደሚኖርባቸው መንፈሳዊ ጥሪ ተላልፏል።  

የጀርመን እና አካባቢው ሀገረ ስብከት ጠቅላላ ጉባኤውን አካሄደ

ታኅሣሥ 18 ቀን 2011 ዓ.ም

በጀርመን ንዑስ ማዕከል

በጥቅምት ወር 2011 ዓ.ም. በተደረገው የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ላይ ለዐራት ተከፍለው በአዲስ መልክ ከተዋቀሩት የአውሮፓ አህጉረ ስብከት አንዱ የሆነው እና በብፅዕ አቡነ ዲዮናስዮስ የሚመራው የጀርመን እና አካባቢው ሀገረ ስብከት የምሥረታ ጠቅላላ ጉባኤውን በፍራንክፈርት ከተማ በሚገኘው በምስካዬ ኅዙናን መድኃኔ ዓለም ቤተ ክርስቲያን ታህሳስ 6 ቀን 2011 ዓ.ም. አካሄደ። ይህ ጀርመንን፣ ስዊዘርላንድን፣ ኦስትሪያን እና ሆላንድን የሚያጠቃልለው ሀገረ ስብከት በቁጥር ከ 30 በላይ የሚሆኑ አጥቢያዎችን የሚያስተዳድር ሲሆን ለዚህ ጉባኤ ከአብዛኛዎቹ አጥቢያዎች የመጡ የአድባራት አስተዳዳሪዎች እንዲሁም የሰበካ ጉባኤ፣ የካህናት እና የሰንበት ትምህርት ቤት ተወካዮች በአጠቃላይ ከ 90 በላይ ተሳታፊዎች ተገኝተውበታል። 

ጉባኤው በጸሎት ከተከፈተ በኋላ የአስተናጋጁ የፍራንክፈርት ምስካዬ ኅዙናን መድኃኔ ዓለም ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ መልአከ መዊዕ ቀሲስ ልሳነወርቅ ውቤ አጭር የእንኳን ደህና መጣችሁ መልዕክት ያስተላለፉ ሲሆን በመቀጠልም ብፁዕ አቡነ ዲዮናስዮስ “መሰባሰባችንን አንተው“ (ዕብ 10÷ 24-25) በሚል ርእስ ተነስተው ስለሀገረ ስብከቱ አወቃቀር እና በመዋቅር ማገልገል ስላለው ጠቀሜታ ሰፊ ማብራሪያ ሰጥተዋል። “የቤተከርስቲያን አንድነት ከመጣ በኋላ የምናደርገው ጉባኤ በመሆኑ በታላቅ ደስታ እንደመጣችሁ አምናለሁ“ ያሉት ብፁዕነታቸው ይህንን አንድነት ለማጽናት በፍቅርና በአንድነት ልናገለግል እንዲሁም ሀገረ ስብከታችንንም ልናጠናክር ይገባል የሚል መልእክት በአጽንዖት አስተላልፈዋል።

በመቀጠል የነበረው መርሐ ግብር የተሰናባቹ የምሥራቅ፣ ምዕራብ እና ደቡብ አውሮፓ ሀገረ ስብከት አስተዳደር ጉባኤ አጭር የሥራ ዘገባ ሲሆን ይህንንም ዘገባ ያቀረቡት የሀገረ ስብከቱ ምክትል ሥራ አስኪያጅ መጋቤ ምሥጢር ኅሩይ ኤርምያስ  ናቸው። አስተዳደር ጉባኤው ከተመረጠበት ከነሐሴ 2005 ዓ.ም. ወዲህ ተሰርተው በም/ሥራ አስኪያጁ ከተዘረዘሩት በርካታ ዐበይት ተግባራት መካከል የቅዱስ ሲኖዶስን እና የጠቅላይ ቤተ ክህነትን መመሪያዎች መፈጸም እና ማስፈጸም፤ የስምንት አዳዲስ አጥቢያዎች መመሥረት፤ የስዊዘርላንድ አጥቢያዎችን ወደ ሀገረ ስብከቱ ማምጣት፤ ኤፍራታ በተባለች ዓመታዊ መጽሔቱ እና በፌስቡክ ገጹ ስብከተ ወንጌለን ማስፋፋት፤ በአድባራት መካካል እና በአድባራት ውስጥ የተከሰቱ አላመግባባቶችን መፍታት፤ ሁለት ዙር የረዳት ሰባክያን ሥልጠና መስጠት፤ ኢትዮጵያ ውስጥ ድርቅ በተከሠተ ጊዜ ከ 20 ሺህ ዩሮ በላይ አሰባስቦ መላክ እና ለጠቅላይ ቤተ ክህነት ዓመታዊ ፈሰስ ማድረግ የሚሉት ተጠቃሽ ክንውኖች ናቸው። በሌላ በኩል ከሀገር ውጭ በነበረው ሲኖዶስ ሥር የነበረው የመላው አውሮፓ ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ መልአከ መዊዕ ቀሲስ ልሳነወርቅ ውቤ ሀገረ ስብከቱ ሲሰራቸው የነበሩትን ዋና ዋና ተግባራት ጠቅለል አድርገው ያቀረቡ ሲሆን ከተለመዱት አድባራትን የመትከል እና ስብከተ ወንጌልን የማስፋፋ ሥራዎች በተጨማሪ በተለይም ከ 5 በላይ አጥቢያዎች የራሳቸው ህንጻ ቤተ ክርስቲያን ባለቤቶች ሆነዋል ብለው ያቀረቡት ክንውን የጉባኤውን  ትኩረት የሳበ ስኬት ነበር።

በሦስተኛነት የተያዘው አጀንዳ ሀገረ ስብከቱን የሚመሩ የአስተዳደር ጉባኤ አባላትን ማስመረጥ ሲሆን ለዚህም በመጀመሪያ የምርጫው ሂደት ምን መሆን እንዳለበት ሰፊ ውይይት ተደርጎበታል። በተለይም የአስተዳደር ጉባኤ አባላቱ ከዐራቱም ሀገራት የተወጣጡ እንዲሆኑ፤ ቀድሞ የሀገር ውስጥ እና የሀገር ውጭ ሲኖዶስ ይባሉ በነበሩት አህጉረ ስብከት ሥር የነበሩትን እንዲሁም ገለልተኛ ይባሉ የነበሩትን አጥቢያዎች ውክልና የሚሰጥ እንዲሆን፤ እንዲሁም ከካህናት በተጨማሪ የምእመናን ተዋጾኦ እንዲኖርበት የሚሉት ቁልፍ ጉዳዮች ላይ ስምምነት ከተደረሰ በኋላ አምስት አባላት ያሉት አስመራጭ ኮሚቴ ተቋቁሞ የምሳ እረፍት ተደርጓል። ከምሳ እረፍት  በኋላ አስመራጭ ኮሚቴው 18 እጩዎችን ያቀረበ ሲሆን ጉባኤው 9 የአስተዳደር ጉባኤ አባላትን በድምጽ ብልጫ መርጧል። ከእነዚህ ውስጥም የፍራንክፈርት ምስካዬ ኅዙናን መድኃኔ ዓለም ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ መልአከ መዊዕ ቀሲስ ልሳነወርቅ የሀገረ ስብከቱ ምክትል ሥራ አስኪያጅ እንዲሁም የፍራንክፈርት ሐመረ ብርሃን ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ ቆሞስ አባ ስብሐት ለአብ የሀገረ ስብከቱ ዋና ጸሐፊ በመሆን ተመርጠዋል።

         

የሀገረ ስብከቱ እና የወረዳ ቤተ ክህነቶች ግንኙነት ምን ይምሰል? የሚለው አጀንዳ ሌላው ጉባኤውን ብዙ ያወያየ አጀንዳ ሲሆን ከአጥቢያዎቹ ቁጥር ማነስ እና የሀገራቱን መልክዐ ምድራዊ አቀማመጥ ግንዛቤ ውስጥ በማስገባት ወረዳ ቤተ ክህነት ማቋቋም ሀብትን እና  የሰው ሃይልን ከማባከን እና የአሰራር ሰንሰለቱን ከማርዘም የዘለለ ብዙ ጥቅም የለውም ያለው ጠቅላላ ጉባኤው ወረዳ ቤተ ክህነት ማቋቋም ሳያስፈልግ አጥቢያዎች በቀጥታ ከሀገረ ስብከቱ ጋር ይገናኙ በማለት ወስኗል።

በመጨረሻም ለተሰናባች የሀገረ ስብከት አስተዳደር ጉባኤ አባላት የምስጋና የምስክር ወረቀት ተሰጥቶ እና ቃለ ጉባኤው ተነቦ ከጸደቀ በኋላ ብፅዕ አቡነ ዲዮናስዮስ የጉባኤውን ተሳታፊዎች እንዲሁም የአስተናጋጁ የፍራንክፈርት ምስካዬ ኅዙናን መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያንን አስተዳዳሪ እና ምእመናንን አመስግነው ጉባኤውን በጸሎት ዘግተዋል።

በሀገረ ጀርመን የካስል ደብረ ቀራንዮ መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን ቅዳሴ ቤት ተከበረ

ኅዳር 5 ቀን 2011 ዓ.ም

በጀርመን ንዑስ ማዕከል

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በጀርመንና አካባቢው ሀገረ ስብከት የካስል ደብረ ቀራንዮ መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን ጥቅምት 24 እና 25 ቀን 2011 ዓ.ም. በሀገረ ስብከቱ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ዲዮናስዮስ ቡራኬ ቅዳሴ ቤቱ ተከበረ። ይህ የሕንጻ ቤተ ክርስቲያን በካህናት እና ምዕመናን ብርቱ ጥረት የተገዛ መሆኑ ታውቋል። በበዓሉም ላይ ተጋባዥ እንግዶች፣ የአድባራት አስተዳዳሪዎች፣ ካህናትና ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን እንዲሁም በርካታ ምዕመናን ተገኝተዋል። Read more