የሕፃኑ የኢየሱስ ልደት

ታኅሣሥ 26 ቀን 2005 ዓ.ም.


ከወልደ ኢየሱስ /ቤካ ፋንታ/

“እነሆ ድንግል ትፀንሳለች ልጅም ትወልዳለች ስሙንም አማኑኤል ትለዋለች” ማቴ.1፥23
ልጆችዬ እንደምን ሰነበታችሁ? ዛሬ ስለ ታላቁ ሕፃን ልደት የምነግራችሁ ነገር አለና በማስተዋል ተከታተሉኝ እሺ፡፡ ጎበዞች!

እንኳን ለብርሃነ ልደቱ በሰላም አደረሳችሁ !!!! | Amharic News & Opinion - Ethiopian  Amharic News

የዛሬ ሁለት ሺ ዓመት ገደማ ነው፡፡ በኢየሩሳሌም ሀገር ንጉሡ ሄሮድስ ሕዝቡን ሁሉ ቤተልሄም ወደምትባል ከተማ ጠራቸው፡፡ እመቤታችንም በዚያ ጊዜ የአሥራ አምስት/15/ ዓመት ልጅ ሆኖ በሚጠብቃት በአረጋዊው /በሽማግሌው/ ዮሴፍ ቤት ትኖር ነበር፡፡ እመቤታችን ድንግል ማርያም ሕፃኑን ኢየሱስ ክርስቶስን ፀንሳ ልትወልድ ደርሳ ሳለ ወደ ቤተልሄም ከተማ ከአረጋዊው ጠባቂዋ ዮሴፍና ከቅድስት ሰሎሜ ጋር ሄደች፡፡ በዚያ ሲደርሱ ምን ሆነ መሰላችሁ? እናታችን ማርያም ቅድስት ሰሎሜና አረጋዊው ዮሴፍ ማደሪያ ፈልገው በየቤቱ እየሄዱ የእግዚአብሔር እንግዶች ነን ማደሪያ ስጡን፣ እባካችሁ አሳድሩን…” ብለው ቢጠይቋቸው ሁሉም “ቦታ የለንም፣ አናሳድርም፣ አናስገባም ሂዱ፡፡” እያሉ መለሷቸው፡፡ በጣም መሽቶ ስለነበረ ጨለማው ያስፈራ ነበረ፣ ብርዱ ደግሞ በጣም ከባድ ነበረ፡፡ ማደሪያ አጥተው የት እንሂድ እያሉ ሲያስቡ ድንገት አረጋዊ ዮሴፍ “ኑ ተከተሉኝ” ብሎ በመንደሩ ውስጥ ወዳለ አንድ የከብቶች ማደሪያ ቤት ወሰዳቸው፡፡ ከከብቶቹ ቤት ሲደርሱ በዚያ አህዮች፣ በሬዎች፣ በጎች፣…. ብዙ እንስሳት ተኝተው አገኙዋቸው፡፡ የበረቱ ሽታ በጣም ያስቸግር ነበረ፡፡ ነገር ግን ማደሪያ ስላልነበረ በዚያ ሊያድሩ ተስማሙ፡፡ ወደ በረቱ ሲገቡ እንስሶቹ ከተኙበት ተነሥተው በደስታ እየዘለሉ ተቀበሏቸው፡፡ በዚያም እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ሕፃኑን ኢየሱስ ክርስቶስን ወለደችው፡፡ ይህም ታላቅ ሕፃን የሁላችንም አምላክ ነው፡፡ ወዲያውኑ የከብቶቹ ቤት በታላቅ ብርሃን ተሞላ፡፡ ቅዱሳን መላእክት ተገለጡ፤ በእመቤታችንም ፊት ሆነው በደስታ ከበሮ እየመቱ፣ እያጨበጨቡ መዘመር ጀመሩ፡፡ መዝሙሩም እንዲህ የሚል ነበር።

“ለእግዚአብሔር ክብርና ምስጋና በሰማያት ይሁን፣ በምድርም ሰላም ለሰውም በጎ ፈቃድ”

ልጆችዬ አሁን አንድ ጥያቄ ልጠይቃችሁ ነው፡፡ ተዘጋጃችሁ? መልካም፡-

• የገናን በዓል እንዴት ነው የምታከብሩት? ለሕፃኑ ለኢየሱስ ክርስቶስ የልደት መዝሙር እየዘመርን ነው አላችሁኝ? ጎበዞች! የገናን በዓል ከወላጆቻችሁ ጋር በቤተ ክርስቲያን ተገኝታችሁ እንደ ቅዱሳን መላእክት በደስታ መዝሙር በመዘመር አክብሩት እሺ፡፡
መልካም የገና በዓል ይሁንላችሁ፡፡

ወላጆች ልጆቻችንን በመንፈሳዊ መንገድ እንዴት እናስተምር?

ዲያቆን ዮሴፍ ከተማ

ወላጆች ለወለድናቸው ልጆች ትልቅ አምላካዊ አደራ አለብን፡፡እግዚአብሔርም ልጅን ያህል ትልቅና የደስታ ምንጭ የሆነ ስጦታ ሲሰጠን ደግሞ ከትልቅ ኃላፊነት ጋር ነው፡፡ ከኃላፊነታችን ትልቁ ለልጅ፡- ሃይማኖትን፤ ምግባርና ትሩፋትን በማስተማር ለእግዚአብሔር መንግሥት እንዲበቃ አድርጎ በፈሪሀ እግዚአብሔር ማሳደግ ነው፡፡ «ልጅን በሚሄድበት መንገድ ምራው፤ በሸመገለም ጊዜ ከእርሱ ፈቀቅ አይልም» እንዲል ምሳ. ፳፪፥፮፡፡

በዘመናችን መንፈሳዊ እሴቶች ተሸርሽረው በአብዛኞቹ ወላጆች «ወልጄ አሳድጌ፤ ወግ ማዕረግ አሳይቼ» የሚሉት የሥጋዊውን ፍላጎት ብቻ በመያዝ ነው፡፡ ዋናው የልጆችም ጥቅም፤ የወላጆችም ኃላፊነት ልጆቻችንን ለክብረ መንግሥተ ሰማያት ማብቃት ነው፡፡ ስለዚህ እያንዳንዱ ወላጅ «ልጄን ለሲኦል ነው ለመንግሥተ ሰማያት ነው የማሳድገው?» ብሎ ራሱን መጠየቅ አለበት፡፡

ማንም ለልጁ ክፉን አይመኝምና ሁሉም ሰው እርሱም ልጆቹም ለክብረ መንግሥቱ እንዲበቁ ይሻል፤ ስለዚህ ልጆች ዛሬ በጥሩ መሠረት ላይ መታነጽ ይኖርባቸዋል፡፡ ልጆች በልጅነታቸው ያልተዘራባቸውን በሕይወታቸው አያፈሩም፡፡አንዳንድ ወላጆች ለዓለማዊ ትምህርት ብቻ ቅድሚያ በመስጠት፤ መንፈሳዊውን ወደ ጎን ይተዋሉ፡፡ መንፈሳዊው ሕይወት ካደጉ በኋላ የሚደርስ ይመስላቸዋል፡፡ በእርግጥ አንዳንድ ወላጆች እኛ ራሳችን የመንፈሳዊ ሕይወት ግንዛቤ ስለሌለን አስፈላጊነቱም እምብዛም አይታየንም ወይንም በሰንበት ቀን ቤተ ክርስቲያን በመሄድ እንገድበዋለን፤ ሁሌ የሚኖሩት ሕይወት መሆኑን አናውቅም፡፡ ይህ ግን ለዚህ ዘመን የልጅ አስተዳደግ አስቸጋሪ ነው፡፡ይህ ዘመን ልጆቻችንን ወስዶ ብኩን የሚያድርጋቸው ብዙ የሕይወት ወጥመድ የሞላበት ነው፡፡ ካደጉ በኋላ በልጅነት የሌላቸውን ለማምጣት ይቸግራል፡፡ «ተስፋ ገና ሳለች ልጅህን ገሥጽ፤ መሞቱንም አትሻ» ምሳ. ፲፱፥፲፰

ስለዚህ የልጆቻችን ዕድገት ሁለንተናዊ እንዲሆን ከዓለማዊ ትምህታቸው ባልተናነሰ ወይንም በበለጠ ለመንፈሳዊው ትምህርትና ሕይወታቸው ከፍተኛ ትኩረትና ጥረት ልንሰጥ ይገባል፡፡ «ሰው ዓለሙን ሁሉ ቢገዛ ነፍሱን ግን ቢያጠፋ ለሰው ምን ይጠቅመዋል?» ማር. ፰፥፴፮፤ ልጆቻችን በአስኳላ (በሳይንስ) ትምህርት ውስጥ ብቻ ቢያልፉ ምዕራባዊ ይሆናሉ፡፡

ምን ማለት ነው?

ዓለማችን በፈጣን ለውጦች ውስጥ እየተጓዘች ነው፡፡ብዙዎች የነሱ ሐሳብ፤እምነት፤ባህልና ሥርዓት በዓለም ላይ እንዲንሰራፋና የዓለም ሕዝብ የነሱ ተከታይ እንዲሆን እየተጉ ይገኛሉ፡፡ በተለይ የምዕራቡ ዓለም በዚህ ረገድ ፊታውራሪ ነው፡፡ሉላዊነት ወይንም ግሎባላይዜሽን በመባል የሚታወቀው የዘመናችን ገዢ ርእዮት ምዕራባዊ ባህልን፤የአኗኗር ዘይቤን በዓለም ላይ ለማሥረጽ የተቀረጸ ነው፡፡የሀገራችን ሥርዓተ ትምህርት ከምዕራባውያን ሥልጣኔ የተቀዳ ነው፡፡

ለመሆኑ ምዕራባዊነት መገለጫውና ግቡ ምድነው?

ምዕራባዊነት በተለይ ልጆችና ታዳጊዎች በሰፊው ተደራሽ በሚሆኑባቸው ፊልም፤ዘፈን፤ የትምህርት ሥዓታችን ወዘተ. በሰፊው የሚሰብክ ሲሆን

፩. ከመንፈሳዊነት ይልቅ ቁሳዊነትን ከፍ አድርጎ የሚያሳይ

፪. ቋሚ የሕይወት ዕሴት የሌለው እንደ ጊዜው የሚለዋወጥ ሰብእና፤ ዓለማዊነትን፤ ግብረ-ሰዶማዊነትን፤ ጾታ መቀየርን፤ የኮንትራት

(በውል በተገደበ ጊዜ ውስጥ የሚጠናቀቅ) ትዳርን ወዘተ

፫. ሃይማኖት የለሽነትን ወይንም ፕሮቴስታንትነትን ግብ አድርጎ የሚሰራ ነው፡፡

ነገር ግን ከላይ በተጠቀሱት መንገዶች ይኸው ሕይወት ከፍ ያለና የሚያስቀና አስመስሎ በቁሳቁስ አጅቦ በማቅረብ የብዙ ወጣቶችን እና ታዳጊዎችን ቀልብ የሚማርክ ሆኗል፡፡ በዚህም አብዛኛው በተለይ የከተማው ወጣት ልቡ መማረኩ በአለባበሱ፤ በምኞቱና በአኗኗሩ ሁሉ የሚታይ ነው፡፡

ምዕራባውያኑ ይህን ዓይነቱን ሁኔታ ለመፍጠር የሚተጉት ለምንድነው? ልብ በሉ! አንድ ማኅበረሰብ የእኛን አኗኗር የሚከተል ከሆነ ሌላው ሁሉ ቀርቶ ቢያንስ በዘላቂነት የእኛን ምርቶች ይጠቀማል፤ በየጊዜው የምናመጣውን አዳዲስ ነገር ይገዛል፡፡ ስለዚህ ዘላቂ የሆነ የገበያ ዕድል ባህላችንን በመሸጥ ብቻ እናገኛለን ማለት ነው፡፡ ይህ የምዕራባውያኑ አንዱ ግብ ሲሆን፤ በፖለቲካ፤ በሃይማኖትና በሌላም መስኮች የዓለም ቁንጮ ሆኖ የመምራትንና ለፈጠራዎቻቸው ሁሉ ተቀባይነትን ያስገኝላቸዋል ማለት ነው፡፡

ምን እናድርግ?

በመሠረቱ ልጆቻችን ላይ የተሠጠንን ኃላፊነት መወጣት የሚገባን ከምዕራባዊነት ልንታደጋቸው ብቻ አይደለም፡፡ ማንነታቸውን በትክክል አውቀው፤ በምድርም በሰማይም ተስፋ ያላቸው፤ ሥጋዊም መንፈሳዊም ዕድገትና ስኬት ያላቸው መሆን ይችሉ ዘንድ ነው፡ ፡

ክረምት

በተለይ ይህ ወቅት ሕፃናትና ታዳጊ ልጆች ብሎም ወጣቶቻች ከመደበኛው ትምህርት በአንጻሩም ነፃ የሚሆኑበት ጊዜ ነው፡፡ ከዚህ በታች ይህን ጊዜያቸውን ሊያውሉበት ይገባል ብለን ያቀረብናቸው ምክረ-ሐሳቦችም በእርግጥ በክረምቱ ጊዜ የበለጠ ቢተገበሩም በበጋውም ቢሆን መዘንጋት የሌለባቸው ነገሮች ናቸው፡፡

ኦርቶዶክሳውያን ልጆች በዚህ ክረምት የበለጠ መንፈሳዊ ሕይወታቸውን ማጎልበት ላይ በማተኮር፤ እግረ መንገዱን ደግሞ ለዘላቂው የክርስትና ሕይወታቸው ስንቅ የሚሆኑ እውቀትና ክህሎቶችን የሚያስጨብጧቸው ጉዳዮች ላይ ማተኮር አለባቸው፡፡ እንደ ምሳሌም

፩. የአብነት ትምህርቶችን ቢከታተሉ

በየደብሩ የአብነትን ትምህርት ከጠቃሚ የአባቶች የሕይወት ምክሮችና ግብረ-ገብ ጋር ጨምረው የሚያስተምሩ ካህናት አሉ፡፡ ልጆች እነዚህን መማራቸው ለጸሎትና አጠቃላይ መንፈሳዊ ሕይወታቸውን ከመጥቀሙም ባሻገር በነገዋ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የአገልግሎት ዕድል ፈንታ ይሰጣቸዋል፤ ይህም ቤተ ክርስቲያናችን ለምትመኘው በሁለት በኩል የተሳለ አገልጋይ ትልቅ መሠረት ነው፡፡ በአገልግሎት ውስጥ መኖር ደግሞ ለሌሎች ከመትረፍም ባሻገር ለራስ መጠበቅ የበለጠ ጠቃሚ ነው፡፡

፪. በሰንበት ትምህርት ቤቶች መርሐ ግብሮች ላይ ቢሳተፉ

እያንዳንዱ ኦርቶዶክሳዊ ልጅ በሰንበት ትምህርት ቤቶች ውስጥ ማለፍ ይኖርበታል፡፡ በጋውንም ጨምሮ ማለት ነው፡፡ ሰንበት ትምህርት ቤት ቤተ ክርስቲያን ሕፃናትን የምትታደግበት አንዱ መዋቅር ነው፡፡ በክረምት ደግሞ በርካታ በአማራጭ የተዘጋጁ መርሐ-ግብሮች ስላሉ ሕፃናት ብዙ ያተርፉባቸዋል፡፡

፫. መንፈሳዊ የዜማ መሣርያዎችን ቢማሩ

በማኅበረ ቅዱሳን ትምህርት ቤቶችና በአንዳንድ ሰንበት ትምህት ቤቶች የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የዜማ መሣርያዎች ሥልጠና በመስጠት ላይ ይገኛል፡፡ እነዚህም በገና፤ መሰንቆ፤ ከበሮና ዋሽንት ናቸው፡፡ ልጆች እነዚህን በዚህ ክረምት ቢማሩ እያደጉ በሄዱ ጊዜ ደግሞ የበለጠ ልምድ ስለሚሆናቸው ባለሙያ ይሆናሉ፡፡ይህም ለአገልግሎት ሕይወትም በር ይከፍትላቸዋል፡፡

፬. መንፈሳዊ ፊልሞችን፤መንፈሳዊ ታሪክና ትምህርት የያዙ የልጆች መጻሕፍትን፤ የሕፃናት መዝሙራትን ወዘተ. መመልከትና ማንበብ ቢችሉ የበለጠ ጠቃሚ ይሆንላቸዋል፡፡ በዚያውም እነዚህን ነገሮች ልምድ እንዲያደርጉ ስለሚረዳቸው ወላጆች ልጆቻቸው በእነዚህ መንገዶች ራሳቸውን በራሳቸው ስለሚያስተምሩ ብዙ ይረዳቸዋል፡፡

እነዚህን ቢያደርጉና በዘላቂነትም ገንዘብ ማድረግ ቢችሉ ለአጠቃላይ ሕይወታቸው ትልቅ ትርጉም ያለው ከመሆኑም ባሻገር ወላጆችም እግዚአብሔር የሚወዳቸውን በጎ ሥራዎች በማድረጋቸው ዋጋ ያገኙበታል፡፡

በመጨረሻም መዘንጋት የሌለበት ልጆች በመንፈሳዊ ሕይወታቸው ጥሩ ሲሆኑ፤ በአስኳላ ትምህርታቸውም የበለጠ ብርቱዎች እንደሚሆኑ የታወቀ ነው፡፡ ይህ ሁኔታ በታችኞቹ ደረጃዎች ሳይወሰን ዛሬ በየዩኒቨርሲቲው በትምህርታቸው ከፍተኛ ውጤት በማስመዝገብ የወርቅ ሜዳሊያና ዋንጫ ሽልማቶቻቸውን ለቤተ ክርስቲያን ሥጦታ የሚያበረክቱ የግቢ ጉባኤ ተማሪዎችን መመልከት በቂ ማስረጃ ነው፡፡

ረድኤተ እግዚአብሔር አይለየን!

መስቀል (ለሕፃናት)

መስከረም 15 ፣ 2013

ብንያም ፍቅረ ማርያም

ምንጭ ማኅበረ ቅዱሳን ዋናው ማዕከል።

እንደምን ሰነበታችሁ ልጆች? እግዚአብሔር ይመስገን፡፡ እንኳን ከዘመነ ዮሐንስ ወደ ዘመነ ማቴዎስ በሰላም አሸጋገራችሁ፡፡ ትምህርት ቤት ተከፍቶ በአዲስ ደብተር፣ በአዲስ እስክርቢቶ፣ በአዲስ ልብስ … ስትማሩ ምን ተሰማችሁ? በጣም ያስደስታል አይደል? ይህ ሁሉ የሆነው እግዚአብሔር አዲስ ዘመን አዲስ ዓመት ስለሰጠን ነው፡፡ መስከረም 17 የሚከበረው የመስቀል በዓልም የእግዚአብሔር ሥጦታ ነው፡፡

 የዘወትር ጸሎት በሚጸለይበት ጊዜ ስለመስቀል እንዲህ የሚል አልሰማችሁም “…መስቀል ኃይላችን ነው፤ ኃይላችን መስቀል ነው፤ የሚያጸናን መስቀል ነው፤ መስቀል ቤዛችን ነው፤ መስቀል የነፍሳችን መዳኛ ነው፡፡ አይሁድ ይክዱታል እኛ ግን እናምነዋለን፡፡ ያመንነው እኛ በመስቀሉ እንድናለን፡፡ ድነናልም፡፡ …” እያልን የምንጸልየው እኛ በጉልበታችን፣ በእውቀታችን ባለን ነገር ሁሉ እንዳንመካ፤ ነገር ግን በመስቀሉ እንድንመካ ነው፡፡

 በመስቀል እንመካለን ምክንያቱም መድኀኔታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከጥንት ጀምሮ ማለትም ከአባታችን አዳም ከእናታችን ሔዋን ጀምሮ እስከ አሁን ጠላታችን የሆነው ዲያብሎስን እንደ ደካማ በመስቀል ተሰቅሎ /ተቸንክሮ/ ድል ስላደረገው፤ አዳምና ሔዋንን ከሲዖል እስራት ነፃ ስላደረጋቸው ነው፡፡ ለእኛም መስቀሉ መመኪያችን ሆኖ ዲያብሎስ መስቀሉን ሲያይ ይሸሸናልና ነው፡፡

 ልጆች መስከረም 17 የምናከብረው የመስቀል ደመራ በዓል ምክንያት አይሁድ መስቀሉ የታመሙትን እንደሚፈውስ፣ የሞቱትን እንደሚያስነሣ ባወቁ ጊዜ በክፉ ቅናት ተነሣሥተው በመስቀሉ ክብር እንዳይገኝ ቆፍረው ቀብረውት፣ ቆሻሻ መጣያም አድርገውት ስለነበር እግዚአብሔርም መስቀሉ ተቀብሮ እንዲቀር ስላልፈለገ ንግሥት እሌኒን አስነሥቶ አባ መቃርስ እና አባ ኪራኮስ በሚባሉ አባቶች መሪነት በቦታው በደረሱ ጊዜ ቦታው ከቆሻሻው ክምር የተነሣ ተራራ ሆኖ ስለነበር ትክክለኛው ቦታ የት እንደሆነ ማወቅ አልቻሉም፡፡

 ንግሥት እሌኒም ወደ እግዚአብሔር በመጸለይዋ የእግዚአብሔር መልአክ ተገልጦላት ደመራ እንድትደምር በዚያም ላይ እጣን እንድትጨምር ስለነገራት አገልጋዮቿን ወታደሮቿን ጠርታ በአካባቢው ደመራ እንዲተክሉ፣ እንዲያቀጣጥሉ፣ እጣንም እንዲጨምሩበት ነገረቻቸው፡፡ በተባሉትም መሠረት አድርገው ጢሱ  ወደሰማይ ከወጣ በኋላ በእግዚአብሔር ኃይል ተመልሶ መስቀሉ ወደ ተቀበረበት ተራራ አመለከተ፡፡ በዚህ ጊዜ ንግሥት እሌኒ እና አገልጋዮቿ ደስ አላቸው፡፡

 ከስድስት ወራት ቁፋሮ በኋላ ሦስት መስቀሎች ተገኙ፡፡ የጌታችን የመድኃኔታችን የኢየሱስ ክርስቶስ መስቀልም የታመሙትን ሲፈውስ ሙት ሲያስነሣ በማየታቸው ከሁለቱ መስቀሎች ለመለየት ችለዋል፡፡ ዲያብሎስ በአይሁድ ላይ አድሮ መስቀሉን ቢደብቅም በእግዚአብሔር ኃይል ሊገኝ ችሏል፡፡ ልጆች መስቀላችሁን አትደብቁ እሺ!

ቸር ሰንብቱ፡፡

ጰራቅሊጦስ (ለሕፃናት)

ሰኔ 14 ቀን 2005 ዓ.ም. በድጋሚ የተለጠፋ በቤካ ፋንታ

  • እግዚአብሔር የሠራት ቀን ይህች ናት/ መዝ 118፥24/

ይህች ታላቅ ዕለት  ከቅድስት ሥላሴ አንዱ አካል የሆነው እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ለቅዱሳን ሐዋርያት፣ ለቅዱሳን አርድእትና ለቅዱሳት ሴቶች የተገለጠባት ዕለት ናት፡፡    እነዚህ ሁሉ በጸሎት ተግተው በሚጸልዩበት ወራት መንፈስ ቅዱስ  በተከፋፈሉ የእሳት ልሳን አምሳል የወረደበት ቅዱስ ቀን ነው፡፡

አስቀድሞ ጌታችን አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለቅዱሳን ሐዋርያት ደብረ ዘይት በተባለ ታላቅ ተራራ ላይ ሳሉ እንዲህ ብሎ አስተምሯቸው ነበር “ኀይልን ከላይ ከአርያም እስክልክላችሁ ድረስ በኢየሩሳሌም በጸሎት ቆዩ፡፡”/ሉቃ 24፡36/ መቶ ሃያው ቤተሰብም በኢየሩሳሌም ሀገር በምትገኝ በቤተ መቅደስ በአንድነት ሆነው በጸሎት በመትጋት ቆዩ፡፡ ልጆችዬ መቶ ሃያው ቤተሰብ የሚባሉት 12ቱ ሐዋርያት፣ 72ቱ አርድእት/አገልጋዮች/ እና 36ቱ ቅዱሳን አንስት/ሴቶች/ ናቸው፡፡

ከዕርገት በኋላ በአሥረኛው ቀን እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ሐዋርያት ወዳሉበት፣ በጸሎትና በምሥጋና ወደ ሚተጉበት ሥፍራ በእሳት አምሳል /ምሳሌ/ ወርዶ በእያንዳንዳቸው ላይ ተቀመጠባቸው፡፡ ይሄንንም  ሁኔታ ተከትሎ  ምስጢር ተገለጠላቸው፣ ይፈሩ የነበሩት ሐዋርያትም ወንጌልን ለማስተማር ደፋሮች ሆኑ፣ በተለያየ ቋንቋዎች እንዲናገሩ እውቀት ተሰጣቸው፤ የእግዚአብሔርንም ጸጋ ተቀበሉ፡፡ ይህንን ታላቅ ኀይል እና ሰማያዊ ስጦታን የሰጣቸውን እግዚአብሔርን በታላቅ ዝማሬና እልልታ አመሰገኑት፡፡

በዓለ ሃምሳ የሚባለውን የአይሁድን በዓል ለማክበር ከተለያዩ ሀገራት የመጡ በጊዜው  የነበሩ ቁጥራቸው በብዙ ሺዎች የሚቆጠሩ  ሰዎች የሐዋርያቱን ታላቅ የዝማሬና የእልልታ ድምፅ ሰሙ፡፡ ከመቶ ሃያው ቤተሰብ መካከል አንዱ የሆነው  ቅዱስ ጴጥሮስ የተሰበሰቡት ሁሉም እንዲሰሙት ድምፁን ከፍ አድርጎ ቃለ እግዚአብሔርን እንዲህ ብሎ አስተማራቸው፡፡ “እናንተ የእስራኤል ሰዎች ሆይ እኛን የሰው ልጆችን ለማዳን እግዚአብሔር ኢየሱስ ክርስቶስ ሰው ሆኖ ወደ ምድር መጥቶ ከክፉ ሥራ ተመለሱ፣ ኀጢአትን አታድርጉ፣ በቅድስና ኑሩ፣ ወደ እኔም ተመለሱ ቢላችሁ፤ እናንተ ግን ምንም በደል ሳይኖርበት ገረፋችሁት፣ አንገላታችሁት፣ በመስቀል ላይም ሰቀላችሁት፡፡ እርሱ ግን እግዚአብሔር ነውና ሞትን ድል አድርጎ ተነሣ፡፡ እርሱ ግን አሁንም ይቅር ባይ ነውና ከኀጢአታችሁ ተመለሱ ንስሐም ግቡ ፡፡” በማለት አስተማራቸው፡፡

የተሰበሰቡት ሰዎች ሁሉ ተገረሙ፡፡ ምክንያቱም ሐዋርያት በፊት የሚያውቁት አንድ ቋንቋ ብቻ ነበረ፡፡ በዚህ ሰዓት ግን ሰባ ሁለት ቋንቋን እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ገልጦላቸው ለሁሉም በየቋንቋቸው አስተማሯቸው፡፡ ይህንንም ድንቅ ተአምር ከተመለከቱት ብዙዎች እግዚአብሔርን አመሰገኑት፡፡ ወደ ሐዋርያትም ቀርበው “አባቶቻችን እናንተ የእግዚአብሔር አገልጋዮች ናችሁና ምከሩን፡፡ እንደ እናንተ የእግዚአብሔር ልጆች እንድንሆንና በቅድስና እንድንኖር ምን እናድርግ?”በማለት ጠየቁ፡ በዚያች ቀን ቁጥራቸው  ሦስት ሺ ያህል ሰዎች በቅዱስ ጴጥሮስ ትምህርት አምነው  ክርስቲያን ለመሆን ቀረቡ፡፡

ቅዱስ ጴጥሮስም እንዲህ አላቸው፡፡ “እነሆ ሁላችሁም ንስሐ ግቡ፡፡ በአምላካችን በኢየሱስ ክርስቶስ የባሕርይ አምላክነት አምናችሁ ተጠመቁ፡፡” አላቸው በዚያው ዕለትም ሦስት ሺ ሰዎች ወደ ሐዋርያት በመቅረብ ኀጢአታቸውን ተናገሩ፤ ሐዋርያትም እግዚአብሔር ይፍታችሁ እያሉ ልጅነትን የሚያሰጣቸውን ጥምቀት አጠመቁዋቸው፡፡

ከዚያ ቀን ጀምሮም በየዓመቱ ይህችን ታላቅ የቤተ ክርስቲያን የልደት ቀን የምትባለውን በዓለ ጰራቅሊጦስን ክርስቲያኖች በታላቅ ደስታና ምሥጋና እናከብራታለን፡፡ እናንተም ልጆችዬ እንደ ቅዱሳን ሐዋርያት በቤተ ክርስቲያን ተገኝታችሁ ቅዳሴ በማስቀደስ፣ መዝሙር በመዘመር እና በመጸለይ ይህችን ታላቅ በዓል ልታከብሯት ይገባል፡፡

የእግዚአብሔር አብ ጸጋ የእግዚአብሔር ወልድ ቸርነት የእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ አንድነት ከሁላችን ጋር ይሁን  አሜን፡፡

በኮሮና ቫይረስ (COVID 19) ሳቢያ በአውሮፓ የምትገኘውን ቤተ ክርስቲያን (ምእመናን) ሊያጋጥሙ የሚችሉ ተግዳሮቶች እና መፍትሔዎች

ሆሣዕና (ለሕፃናት)

በቤካ ፋንታ

03.08.2012

በኢየሩሳሌም በምትገኝ በአንድ ትንሽ መንደር ውስጥ ነው የምኖረው፡፡ ከተወለድኩ አምስት ዓመት ሞልቶኛል፡፡ በዕለተ ሰንበት በቤት ውስጥ እየተጫወትሁ፣ እናቴም በጓዳ ሥራ እየሠራች ሳለን በድንገት የብዙ ሰዎች የዕልልታ ድምፅ በሰፈሩ ውስጥ ሰማን፡፡ እናቴም በፍጥነት ከጓዳ ሮጣ ወጥታ ‹‹ልጄ! ልጄ! ነይ እንሒድ!›› ብላ አዝላኝ እየሮጠች ከቤት ወጣች፡፡ በኹኔታው ተገርሜአለሁ፡፡

በሰፈር ውስጥ ያሉ ጓደኞቼ ዅሉ በእናቶቻቸው ጀርባና በአባቶቻቸው ትከሻ ላይ ኾነው ከወላጆቻቸው ጋር በደስታ ዕልል ይላሉ፡፡ የሕፃናቶቹን ብዛት ሳይ ይበልጥ ተደሰትሁ፡፡ የሚያለቅስ አንድም ልጅ የለም፡፡ ‹‹ዛሬ የሕፃናት የደስታ እና የዝማሬ ቀን ነው›› ብሎ ልቤ በደስታ ፈነደቀ፡፡ ወላጆቻችን ዅሉ የዘንባባ ዝንጣፊ እየቈረጡ ያዙ፤ ለእኛም ሰጡን፡፡ ከዚያ ዕልል እያልን በደስታ ወደ ቤተ መቅደስ ሮጥን፡፡

በመንገድ ላይ በጣም ብዙ ሕዝብ አየሁ፤ እነርሱም ዘንባባ ይዘው ደስ ብሏቸው እንደኛ ወደ ቤተ መቅደስ ይሮጣሉ፡፡ በመካከላቸው አንድ ትልቅ አህያ አየሁኝ፣ ከአህያይቱም ጋር ውርንጫዋ (ልጇ) አለች፡፡ የሚያማምር ልብስ በአህያዎቹ ጀርባ ላይ ተነጥፏል፡፡ በውርንጫዋም ላይ የዅላችን ፈጣሪ፣ ንጉሣችን፣ አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተቀምጦ ስመለከት በደስታ ዘለልሁኝ፡፡

ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር መኾን በጣም ያስደስታል፡፡ ምክንያቱም እርሱ እኛ ሕፃናትን እቅፍ አድርጎ ስሞን በጉልበቱ ላይ ቁጭ አድርጎ ያስተምረናል፣ ይመክረናል፡፡ በዙሪያውም ላሉት ሰዎች ‹‹እንደነዚህ ሕፃናት ንጹሓን ኹኑ፤ ኃጢአት አትሥሩ፤›› እያለ ይመክራቸዋል፡፡

ከዚያ ዕልል እያለ የሚያመሰግነው ሕዝብ፣ እንደዚሁም በእናትና በአባቶቻችን እቅፍ ውስጥ ያለን ሕፃናት በአንድነት ኾነን ጮክ ብለን የዘንባባውን ቅጠል እያውለበለብን መዝሙር መዘመር ጀመርን፡፡ መዝሙሩም እንዲህ የሚል ነው፤ ‹‹ሆሣዕና በአርያም ለዳዊት ልጅ፤ በጌታ ስም የሚመጣ የተባረከ ነው፡፡ ሆሣዕና በአርያም፤ ሆሣዕና በአርያም፤ ሆሣዕና በአርያም፡፡›› የመዝሙሩ ድምፅ በኢየሩሳሌም ከተማ ከጫፍ እስከ ጫፍ ተሰማ፡፡ በጣም ደስ ያለኝ ደግሞ የእኛ የሕፃናቱ ድምፅ ከትልልቆቹ በልጦ መሰማቱ ነው፡፡

ጌታችንን በአህያዋ ላይ ተቀምጦ ባየሁት ጊዜ ትዝ ያለኝን አባዬ መጽሐፍ ቅዱስ እያነበበ ያስተማረኝን ታሪክ ልንገራችሁ፤ ታሪኩም፡- ‹‹አንቺ የጽዮን ልጅ ሆይ፣ እጅግ ደስ ይበልሽ! አንቺ የኢየሩሳሌም ልጅ ሆይ፣ ዕልል በዪ! እነሆ ንጉሥሽ ጻድቅና አዳኝ ነው፤ ትሑትም ኾ በአህያ፣ በአህያይቱም ግልገል በውርንጫይቱ ላይ ተቀምጦ ወደ አንቺ ይመጣል፤›› የሚል ነው (ትንቢተ ዘካርያስ ፱፥፱)፡፡

የዝማሬውን ድምፅ ሲሰሙ አምላካችንን ኢየሱስ ክርስቶስን የማይወዱት በከተማው ውስጥ ያሉ ጨካኝ ሰዎች ወደ እኛ መጡ፡፡ ሰዎቹም ሕዝቡ ዅሉ ደስ ብሏቸው እየዘመሩ፣ ዕልል እያሉ፣ የዘንባባውን ቅጠል እያውለበለቡ፣ ኢየሱስ ክርስቶስን እያመሰገኑ ወደ ቤተ መቅደስ ሲሔዱ በተመለከቱ ጊዜ ተናደው ሕዝቡን ‹‹ዝም በሉ!›› ብለው ተቈጧቸው፡፡ ሕዝቡም ፈርትው ዝም አሉ፡፡

እኔና ጓደኞቼ ግን በእናታችን ጀርባ ላይ ካሉት ሕፃናት ጋር አብረን ኾነን ጮክ ብለን ‹‹ሆሣዕና በአርያም›› የሚለውን መዝሙር ሳናቋርጥ እንዘምር ነበር፡፡ የገረመኝ ደግሞ ከእኔ የሚያንሱ ሕፃናትም መዝሙሩን ጮክ ብለው ሲዘምሩት መስማቴ ነው፡፡ ‹‹እግዚአብሔር ሆይ መናገር የማንችለውን እኛን እንድንዘምርልህ ስለፈቀድህልን ተመስገን!›› ብዬ አምላኬን አመስግኜ መዝሙሩን መዘመር ቀጠልሁኝ፤ ‹‹ሆሣዕና፣ ሆሣዕና፣ ሆሣዕና በአርያም …፡፡››

በኋላ ግን እነዚያ ጨካኞቹ ሰዎች ስላስፈራሯቸው ወላጆቻችን ዝም አስባሉን፡፡ ጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም በአህያዋ ውርንጫ (በትንሿ አህያ) ላይ ቁጭ ብሎ ለጨካኞቹ ሰዎች ‹‹ከሕፃናት ከሚጠቡት አፍ ምስጋናን ለራሴ አዘጋጅቻለሁ፡፡ የእነርሱንም አፍ ይዛችሁ ዝም ብታስብሏቸው በዙሪያዬ ያሉት ድንጋዮች ያመሰግኑኛል፤›› አላቸው፡፡

ከዚያም ጌታችን፡- ‹‹የፈጠርኋችሁ ድንጋዮች ሆይ! ሕፃናት እንደ ዘመሩ እናንተም በመዝሙር አመስግኑኝ፤›› በማለት በታላቅ ድምፅ ሲናገር ግዙፍ ድንጋዮች ከመሬት ወደ ላይ እየተነሡ ‹‹ሆሣዕና በአርያም ለዳዊት ልጅ ለኢየሱስ ክርስቶስ ምስጋና እናቀርባለን …›› እያሉ በሚያስደስት ድምፅ እየመዘመሩ እግዚአብሔርን አመሰገኑ፡፡ በዚህ ጊዜ ጨካኞቹ ሰዎች አፍረውና ፈርትው ተመለሱ፡፡

እኛ ሕፃናት፣ ወላጆቻችንና በዙሪያችን የነበሩ ድንጋዮችም አምላካችንን ከበን በዕልልታ እየዘመርን፤ ለአህያዎቹ መርገጫ ልብሳችንንና የዘንባባውን ዝንጣፊ እያነጠፍን ወደ ቤተ መቅደስ ገባን፡፡ በዚያም ፈጣሪያችን ኢየሱስ ክርስቶስ ደስ የሚል ትምህርት አስተማረን፡፡

በመጨረሻም ‹‹ሆሣዕና›› ብለን ምስጋና ላቀረብነውና በቤተ መቅደስ ተገኝተን ቃሉን ለምንሰማው ሕፃናት ጌታችን እንዲህ ብሎ መከረን፤ ‹‹ልጆቼ በመዝሙራችሁ ተደስቻለሁ፡፡ ዅል ጊዜ ወደ ቤተ ክርስቲያን እየመጣችሁ ዘምሩልኝ፡፡ በአንደበታችሁ በመዝሙር አግዚአብሔርን አመስግኑበት እንጂ ዘፈን እንዳትዘፍኑበት፡፡ ዘፈን ኃጢአት ነው፡፡››

ትምህርቱን ተከታትለን ከእናቴ ጋር ደስ እያለን ወደ ቤታችን ተመለስን፡፡ ታዲያ ዅል ጊዜ ይህችን የሆሣዕናን በዓል በውስጤ አስባታለሁ፤ መዝሙሩን መዘመር በጣም ያስደስተኛል፡፡ አምላኬ ኢየሱስ ክርስቶስ በመጨረሻ የመከረኝንም ምክር ጠብቄ ዘፈን የሚባል በአፌ ሳልዘፍን በመዝሙር እግዚአብሔርን እያመሰገንሁ አደጌአለሁ፡፡

ልጆችዬ! ዛሬ የምታነቡት የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል የማቴዎስ ወንጌል ምዕራፍ ፳፩ ከቍጥር ፩ እስከ ፲፮ እና የማርቆስ ወንጌል ምዕራፍ ፲፩ ከቍጥር ፩ እስከ ፲፯ ያለው ትምህርት ነው፡፡

‹‹ሆሣዕና በአርያም›› ብለን እንድናመሰግነው የፈቀደልን፤ ኃይሉን ጥበቡን የሰጠን አምላካችን ልዑል እግዚአብሔር የተመሰገነ ይኹን!

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

የቤተልሔም እንስሳት

ታኅሣሥ 2003 , ስምዐ ጽድቅ

እንደምን ሰነበታችሁ ልጆች

ልጆች ቤተልሔምን ታውቋታላችሁ?ቤተልሔም ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተወለደባት ከተማ ናት። እና ልጆች የቤተልሔም እንስሳት ጌታችን መወለዱን በሰሙ ጊዜ እጅግ ተደስተው “ምን ይዘን እንሂድ? ምንስ እናበርክት?”በማለት በሬዎች፥በጎች፥ጥጃዎች፥ህያዎችና ሌሎች እንስሳት ተሰብስበው መወያየት ጀመሩ።


ፀሐይ ልጆቿን ጨረቃንና ከዋክብትን ጠርታ “ልጆቼ ሆይ ዛሬ ታላቅ ደስታ በኢየሩሳሌም ሀገር በቤተልሔም ከተማ ተፈጽሟል።የዓለም ፈጣሪ ጌታችን ተወልዷልና ፍጥረታት ሁሉ በደስታ የምንዘምርበት ቀን ነው።እና ልጆቼ የጥበብ ሰዎች /ሰበዓ ሰገል / ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መወለዱን ሰምተው ከሩቅ ሀገር ተነስተው መምጣት ፈልገዋልና ከእናንተ መኻከል ማነው ጎበዝ እነዚህን ክቡር እንግዶች ፈጥኖ ይዟቸው የሚመጣው?” ስትል ጠየቀቻቸው። ሁሉም ‘እኔ ልላክ እኔ ልላክ”እያሉ ሲያስቸግሯት እናታቸው ፀሐይ ዕጣ አውጥታ ለአንዷ ኮከብ ደረሳት። ዕጣ የወጣላት ኮከብ ከደስታዋ ብዛት በሰፊው ሰማይ ላይ ክብልል እያለች እየበረረች እንግዶቹ ዘንድ ደረሰች።እንግዶቹም ለታላቁ ጌታችን የምናበረክተው ስጦታ ብለው ዕጣን፥ ወርቅ፥ከርቤ ይዘውለት ሲመጡ አገኘቻቸው።ኮከቧ በጣም ደስ አላትና ቦግ ብላ በራች።ወደ ቤተልሔምም እየመራቻቸው ሔደች።


ጌታችን በተወለደባት ሌሊት በቤተ ልሔም ከተማ አካባቢ ከብቶቻቸውን ሲጠብቁ ያደሩ እረኞች ነበሩ።የጌታ መልአክ ወደእነርሱ ቀረበ። ወዲያውም ያሉበት ቦታ በብርሃን ተጥለቀለቀ። በዚህ ጨለማ የምን ብርሃን ነው የምናየው? ብለው ፈርተው ሊሸሹ ሲሉ የእግዚአብሔር መልአክ “አይዟችሁ ልጆች፥እነሆ ለህዝብ ሁሉ የሚሆን ታላቅ ደስታ የምስራች እነግራችኋለሁና አትፍሩ።ይህም ምልክት ይሆንላችኋል።ህፃን በጨርቅ ተጠቅልሎ ተኝቶ ታገኛላችሁ።” አላቸው። ብዙ የሰማይ ሰራዊትከመለኩ ጋር ነበሩ። እግዚአብሔርንም እያመሰገኑ “ክብር ለእግዚአብሔር በአርያም ይሁን ሰላምም በምድር ለሰውም በጎ ፍቃድ።” አሉ። ልጆች ይገርማችኋል የዚያን እለት አበባዎች በደስታ አበቡ።እፅዋት ለመለሙ።ንቦችም ማራቸውን ሰጡ። የቤተልሕውም እንስሳት እኛስ ምን እንስጥ እያሉ ግራ ገባቸው። በመጨረሻ አህያ ከሁሉም የበለጠ አሳብ አመጣች። “ጌታችን የተወለደው በበረት ነው አይደል?” ስትል ጠየቀቻቸው። “አዎን” አሏት። “ታዲያ እኮ ልብስ የለውም።ደግሞም እንደምታዩት ጊዜው ብርድ የበዛበት ነው።” አለች። “እና አህያ ምናችን ልብስ ይሆነዋል ብለሽ አሰብሽ?” አሏት “ለምን ትንፋሻችንን አንሰጥም?”አለች። ሁሉም በጣም ደስ አላቸው።እንስሳቱ ትንፋሻቸውን ሊያበረክቱለት ጌታችን ወደተወለደበት በረት እየሮጡ ሄዱ። ልጆች እናንተም ደስ ካላቸው ጋር አብራችሁ ደስተኞች እንድትሆኑ ባላችሁ ነገር ሁሉ
ስስታም አትሁኑ። እሺ ልጆች።


++++++
ምንጭ፥ ጥበበኛው ሕፃን
የሸዋ ወርቅ ወልደ ገብርኤል

“ስብሐት ለእግዚአብሔር በሰማያት ወሰላም በምድር ሥምረቱ ለሰብእ፤ በሰማያት ምስጋና ተደረገ በምድርም እርቅ ተወጠነ ‹‹ሰላም ሆነ፡፡›› (ሉቃ. ፪፥፲፬)

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን፡፡

እንኳን ለብርሃነ ልደቱ በሰላም አደረሳችሁ!

ለአዳም የሰጠውን ተስፋ ሊፈጽም በነቢያት አድሮ ያናገረው ትንቢት ሲደርስ ሰው የሆነ አምላክ የተወለደበት ዕለት (የልደት በዓል) እነሆ ደረሰና እኛም በዓሉን አክብረን ከበረከተ ልደቱ እንድንሳተፍ አበቃን፡፡

አምላካችን ለእኛ ላደረገልንና ለሚያደርግልን የቸርነት ሥራው ሁሉ ከምስጋና በቀር ሌላ አቅም ኖሮን መክፈል የምንችለው ነገር የለንም፡፡ ምክንያቱም እንክፈል ብንልም እንኳን ከእርሱ ያላገኘነው ምንም ነገር የለንምና፡፡ ከሕይወታችን ጀምሮ ሁሉንም ነገር ያገኘነው ከእርሱ ነውና፡፡ የሰዎች ልደት የሚከበረው በሕይወት ዘመናቸው ሲሆን ከሞቱ በኋላ የሚከበረው ግን ሙት ዓመታቸው ነው፡፡ አምላካችን ግን ልደቱም፣ ሞቱም ከተወለደበት እስከ ዐረገበት ጊዜ ድረስ ተአምራት ያደረገባቸው ቀናት ሁሉ ሁሌም እንደ አዲስ ይከበራሉ እኛ የምንኖረው ለራሳችን ሲሆን እርሱ ግን ሁሉንም ያደረገው ለሰው ልጆች ደኅንነት በመሆኑ ልደቱን በምናከብርበት ጊዜ ደኅንነታችንን እያሰብን ሲሆን በረከትን እናገኛለን፡፡

ጌታችን ሲወለድ እውነተኛው ሰላም እንደሚገኝና ፍጹም ደኅንነት እንደሚደረግ ነቢያት አስቀድመው በተናገሩት መሠረት በተወለደበት ዕለት መላእክትና እረኞች በአንድነት ሆነው “በሰማያት ምስጋና ይሁን በምድርም እርቅ ተወጠነ ‹‹ሰላም ሆነ›› ብለው አመሰገኑ፡፡ ይህ ብሥራት በሰውና በእግዚአብሔር መካከል እርቅ እንደተወጠነ ‹‹ሰላም እንደሰፈነ›› ያስረዳል፡፡ የመላእክትና የእረኞች ምስጋና አምላክ ሲወለድ የተገኘውን ሰላም ታላቅነት ያስረዳናል ምክንያቱም ሰላም ከሌለ ምንም አይኖርምና፡፡

አንድ አዳም በፈጸመው ስሕተት ምክንያት ፶፻ወ፭፻ (አምስት ሺህ አምስት መቶ ዓመት) ዘመናት ያህል የሰው ልጆች ሁሉ ሰላማችን ጠፍቶ በጨለማና በሞት ጥላ ሥር እንድንኖር ተገደን ነበር፡፡ አምላካችን የተወሰደብንን ሰላማችንን ሊመልስልን ፈቃዱ ሆኖ የእኛን ሥጋ በመዋሐድ ሰው ሆኖ በተወለደባት ዕለት ይህን የምሥራች የሚያበሥር የምስጋና ዝማሬ መላእክትና እረኞች በአንድነት ዘመሩ፡፡

ጌታችን በወንጌል “ሰላሜን እሰጣችኋለሁ እኔ የምሰጣችሁ ሰላም ዓለም እንደሚሰጣችሁ አይደለም፡፡” (ዮሐ. ፲፬፥፳፯) በማለት እውነተኛው ሰላም የሚገኘው ከእርሱ ብቻ መሆኑን ነግሮናል፡፡ አምላካችን ሰላምን የተወልን ራሱን ለሞት አሳልፎ በመስጠት ነው፡፡ ዛሬ ዓለም ሰላምን ለማምጣት የሚከተለው መንገድ ከዚህ በተለየና በተቃራኒው ነው፡፡ ሌላውን አጥፍቶ እየኖረ ሰላም አገኘሁ ይላል፡፡

ሰላም በሥጋዊ ኃይል የሚመጣ በወረቀት ላይ ብቻ የሚሰፍር በአንደበት የሚለፈፍ አይደለም፡፡ ሰላም ከሰዎች የሚሰጥ ገጸ በረከት ሳይሆን ከውስጣችን የሚገኝ ሕይወት ነው፡፡ ሰላም በመተሳሰብ፣ በመግባባትና በፍቅር የሚመጣ የጤናማ ውይይት ውጤት ነው፡፡ ሰላም የውስጥ እፎይታ የመንፈስ እርካታ የኅሊና እረፍት ነው፡፡ ሰላም በዋጋ የማይተመን ከነገሮች ሁሉ የበለጠ ታላቅ ቁም ነገር ነው፡፡

አምላካችን የሰጠን ሰላም በሰዎች ሥጋዊ አስተሳሰብ ያልሆነና የእግዚአብሔር የሆኑት ብቻ የሚኖሩበት ሕይወት ነው፡፡ ሰዎች የጠፋ ሰላማቸውን ለማግኘት በራሳቸው መንገድ ብዙ ሲደክሙና መውጣት ለማይችሉባቸው ብዙ አጓጉል ሱሶችም ራሳቸውን አሳልፈው ሲሰጡ ይስተዋላሉ፡፡ ሰላም በራስ ኅሊና ውስጥ በትዳር መካከል በቤተሰብ መካከል በሥራ ቦታ በሀገር ውስጥ ሊታጣ ይችላል፡፡ እግዚአብሔርን የያዘ ግን የትም ቢሔድ ሰላም አለው፡፡ ሰላም የራስ የሆነ ማንም የማይቀማው ከእግዚአብሔር የሚገኝ ሀብት ነውና፡፡

ዛሬ ዓለም ያልተረዳውና ሊኖርበት ያልቻለው ይህን ዕውቀት ነው፡፡ በዚህ ሰላማዊ ሕይወት ኖረው ያለፉ የቀደሙ ሰዎችን የሃይማኖት ጉዞ እንደ ሞኝነት ዘመን እየቆጠረ ራሱን ሲያሞኝ ይታያል፡፡ዓለማችን ለሰላም የቆመ ይመስል ቆሜያለሁ እርስ በእርሱ የሚጠፋፋበትን ከባድ መሳሪያ በማምረት ሥራ ላይ ተጠምዷል፡፡ ሰላሙን ማረጋገጥ የሚፈልገውም ባለው የኃይል ሚዛን ሆኗል፡፡ ሰላም በንግግርና በምኞት ብቻ የሚመጣ ሳይሆን በተግባር የሚገለጥ እውነት መሆኑን ረስቶ ተቃራኒውንና የመጠፋፊያውን አቋራጭ መንገድ ተያይዞታል፡፡ ይህ ሁሉ የሚሆነው ሰው በራሱ ዕውቀት ብቻ በመመራቱ እና የእግዚአብሔርን ቦታ ለመተካት በመፈለጉ ነው፡፡

የሰው ሕይወት ያለ እግዚአብሔር ሙሉ አይሆንም፡፡ እግዚአብሔር የሌለው ሰው በውስጡ ባዶነት ይሰማዋል፡፡ ስለሆነም ይበላል ይጠጣል ግን አይረካም፣ ይለብሳል ግን አይደምቅም፣ ይናገራል ግን እርስ በእርሱ አይግባባም፣ ይሮጣል ግን ማንንም አይቀድምም፡፡ (ሐጌ. ፩፥፭) የተመኘውን ሁሉ ለማድረግ ይጣደፋል፡፡ በዚህ ሁሉ ሰላም የለውም፡፡ ይህ የሚሆነው በውስጡ እውነተኛው ሰላም ክርስቶስ ስለሌለው ነው፡፡የጌታችንን ልደት ስናከብር ፍቅርን፣ ሰላምን፣ ራስን ለሌላው አሳልፎ መስጠትን፣ ይቅር መባባልን በማሰብ ሊሆን ይገባል፡፡ ዓለማችን ያለችበት ሁኔታ አደገኛና እጅግ ፈታኝ የሆነ ወቅት ነው፡፡ ሁሉም የራሱን ጩኸት እንጂ የሌላውን ሐሳብ የሚያዳምጥበት ጆሮ የለውም፡፡ ጌታችን በተወለደበት ዕለት ሰብአ ሰገል (የምሥራቅ ነገሥታት) ከርቀት ቦታ በኮከብ እየተመሩ መጥተው ለጌታችን ከሰገዱለት በኋላ ወርቅ፣ ዕጣን፣ ከርቤ (እጅ መንሻ) አቅርበውለታል፡፡ (መዝ. ፸፩፥፱-፲፩)

በሌላ በኩል ደግሞ ሄሮድስ የተባለው ንጉሥ ጌታን ሊገድለው ይፈልገው ነበር፡፡ ‹‹ታሪክ ራሱን ይደግማል›› ሆነና ዛሬ ዓለማችን አንዱ ለመልካም ሌላው ደግሞ ለጥፋት ተልዕኮ የሚጣደፉባት መድረክ ሆናለች፡፡በዓሉን በምናከብርበት ወቅት በዓለም ላሉ መሪዎች ሁሉ እግዚአብሔር እንደ ሄሮድስ ያለውን የድንጋይ ልብ አውጥቶ እርሱን መፍራትና ማስተዋልን እንዲሰጣቸው ልንጸልይላቸው ይገባል፡፡

የዛሬዋ ዓለማችን ፈሪሃ እግዚአብሔር የሌላቸው በጡንቻቸው የሚመኩ ከወገንና ከሀገር ይልቅ ለራሳቸው ሥልጣንና ዝና ቅድሚያ የሚሰጡ መሪዎች ስለበዙባት የግፍና የሰቆቃ ዓለም ሆናለች፡፡ የሰው ልጅ ኑሮም የተረበሸና መረጋጋት የጠፋበት ሆኗል፡፡ሰላም በድሃውም በሀብታሙም ቤት ባደጉትም በድሆችም ሀገሮች በትንሹም በትልቁም ሕዝብ መካከል ጠፍቷል፡፡ በዓለም ዙሪያ ያለውና በየቀኑ የሚሰማው ሁሉ ተስፋ አስቆራጭ እየሆነ መጥቷል፡፡ ዓለም ለመጠፋፋት የሚያውለውን ጊዜ መልካም ወደማድረግ መለወጥ አለበት፡፡

ሰላም ከሌለ ሕፃናት ወጥተው መግባት፣ ሠራተኛው ሠርቶ መኖር፣ ነጋዴው ነግዶ ማትረፍ፣ ገበሬው አምርቶ መኖር አይችልም፡፡ ሰዎች ሁሉ አምላካችን ወደዚህ ዓለም የመጣው ሰላምን ለሰው ልጆች ለመስጠት መሆኑን ተረድተው ለሰላም በጎ ምላሽ ሊሰጡ ይገባል ለሁሉም መሠረቱ ሰላም ነውና፡፡ሄሮድስም ጌታን ያገኘው መስሎት እስከ ሁለት ዓመት ዕድሜ ያላቸውን ዐሥራ አራት ሺህ ሕፃናት ልብስና ቀለብ እሰጣለሁ ብሎ ሰብስቦ በጭካኔ በሰይፍ አስገደላቸው፡፡ የእርሱ ሐሳብ ጌታን ገድሎ እንደ ልቡ በሥልጣን ላይ ለመኖር ነበር፡፡ ነገር ግን ጌታንም አላገኘውም፣ በሥልጣኑ ላይም አልቆየበትም፡፡ ሰው እግዚአብሔርን ካልፈራ ለጭካኔው ገደብ የለውም፡፡ ሥጋዊ ጥቅም እስካገኘለት ድረስ በእርሱ አስተሳሰብ ሰውን መግደልም ትክክል ነው፡፡

መሪዎች ቆም ብለው ማሰብ ቢችሉ እኮ ሁሉም እንደሚያልፍ መረዳት ይችሉ ነበር፡፡ ነገር ግን ቀና መንፈስ እና የተሰበረ ልብ የሚገኘው ከእግዚአብሔር ስለሆነ እነርሱም ያወቁ መስሏቸው አምላክን ትተው በራሳቸው ዕውቀትና ኃይል በመተማመናቸው ማጣፊያው አጠረባቸው፡፡ የሰው ልጅ ሁሉንም አውቃለሁ ብሎ ካሰበ መጨረሻው ጥፋት ነው፡፡ ከሁሉ በላይ የሆነ አምላክ ብቻ እንደሆነና ነግሮች ሁሉ የሚከናወኑት በአምላክ ጥበብና ፈቃድ መሆኑን መረዳት አለበት፡፡ ባይረዳም ግን ነገሮች እንዲህ ከመሆን አይቀሩም፡፡ ሰው ቢችል ኖሮ በሽታንም፣ ድህነትንም፣ ጦርነትንም፣ የማያስፈልጉ ነገሮችን ሁሉ ማጥፋት ይችል ነበር፡፡ ሁሉም ነገር ከሰው ልጅ አቅም በላይ በመሆኑ (መድኃኒት የሌለው በሽታ ማቆሚያ የሌለው ጦርነት፣ የሥራ አጥ ብዛትና የኢኮኖሚ አለመረጋጋት) የመሳሰሉ አደጋዎች ውስጥ ገብቷል፡፡ 

የእግዚአብሔር ቃል ሁሉም ነገር በአምላክ ፈቃድ እንደሚደረግ ያለ እርሱ ፈቃድ አንዳችም እንዳልሆነና እንደማይሆን ይናገራል፡፡ ዓለም ደግሞ ለችግሮች ሁሉ መልስ ይሰጣል በሚለው ጥበቡ ስለተማመነ ይህን ቃል ለማዳመጥ ጆሮ የለውም፡፡ ዕውቀቱ ግን ችግሮችን ሲያባብስ እንጂ መፍትሔ ሲሰጥ አይታይም፡፡እግዚአብሔር የሌለበት ዕውቀት… መጨረሻው ጥፋት ነው፡፡ በጌታችን ልደት ዕለት መላእክትና እረኞቹ ሲያመሰግኑ በሄሮድስ ቤተ መንግሥት ግን የጥፋት ሸንጎ ተይዞ ጌታን ስለመግደል ይዶለት ነበር፡፡

እንደዚያ ጊዜው ሁሉ ዛሬም ምእመናን በቤተ ክርስቲያን ተገኝተው የልደትን በዓል በዝማሬና በምስጋና ሲያከብሩ፣ ሌሎቹ ደግሞ በመንፈሳዊው በዓለ ልደት ስም ፓርቲ አዘጋጅተው በመጨፈርና በመዳራት ያሳልፋሉ፡፡ ለክብር የተፈጠረውን ሰውነታቸውንና አክብረው ሊከብሩበት የተዘጋጀላቸውን ቅዱስ በዓል ጨፍረውም ሆነ አብደው ለማይረኩበትና የውስጣቸውን ጉድለት እንዲያስረሳቸው እንደማደንዘዣነት ለሚጠቀሙበት ጊዜያዊ ፍላጎታቸው ያውሉታል፡፡ ያም ቢሆን ስላመኑበት ብቻ ያደርጉታል እንጂ ሲረኩበት አይታዩም፡፡

ጌታችን በተወለደበት በረት ውስጥ የነበሩት እንስሳት በትንፋሻቸው አሟሙቀውታል ወቅቱ (ታኅሣሥ ወር) በፍልስጥኤም ምድር የብርድ ወቅት ነበርና፡፡ ጌታችን በዚህ አስቸጋሪ ወቅትና በማይመች ሁኔታ መወለዱ እኛን ለማዳን ባደረገው ጉዞው ሁሉ ፍጹም ፍቅሩን ሊገልጽልንና በእኛ ተገብቶ ባደረገው ሥራውም በአዳም በደል ምክንያት ተጥለን ለነበርን ለእኛ የሰው ልጆች ሁሉ በመካስና ከውድቀታችን በማንሳት ፍቅሩን ሊገልጽልን ስለወደደ ነው፡፡

መላእክትንና እረኞችን ለምስጋና የመረጠ ሰብአ ሰገልን ስጦታ ለማቅረብ ያበቃ አምላክ የእኛንም የምስጋና መዝሙርና አገልግሎት የተወደደ መሥዋዕት አድርጎ ይቀበልልን፡፡ አሜን!! !ወስብሐት ለእግዚአብሔር!

ሁለቱ እንስሶች

በአስናቀች ታመነ

ምንጭ: ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ ከሰኔ 16 – 30/ 2011 ዓ.ም. ዕትም

ሰላም ልጆች እንደምን አላችሁ? ደኅና ናችሁ ለዚህ ቀን ያደረሰን እግዚአብሔር ይመስገን! አሜን! ልጆች ዛሬ ከሌላው ቀናት የተለየ ታሪክ ይዘንላችሁ ቀርበናል። ጽሑፉን ከማንበባችሁ በፊት አስቀድማችሁ እስቲ ገምቱ ስለምን ይመስላችኋል፧ ስለቅዱሳን ሰዎች ካላችሁ እንደዛ አይደለም። ስለምን እንደሆነ ልንገራችሁ ስለ እንስሳት ነው። ስለየትኞቹ እንስሳት ካላችሁኝ ስለ አያ አንበሶ እና የሚጣፍጥ ማር ስለምትሰጠን ስለ ንብ ነው።

አያ አንበሶ

ከእለታት አንድ ቀን በቅድስት ማርያም ገዳም የንግሥ በዓል ይሆንና ብዙ ምእመናን በዓሉን ለማክበር ወደ እመቤታችን ቤተክርስቲያን ይመጣሉ። በንግሥ በዓሉ ላይ የተገኘው ሕዝበ ክርስቲያን ያለውን ሁሉ በደስታ ይሰጥ ጀመር። አንድአንዱ ገንዘቡን ፣ አንድአንዱ ደግሞ የአንገት ጌጡን ፣ ሌላው ደግሞ የእጅ ወርቁን ፣ ልብስ ፣ ጧፍ ፣ ሻማ ፣ ዕጣን ይሰጣል። ይህን የተመለከተ አንድ ሰው ፍቅረ ነዋይ ያድርበትና ይህን ብርና ወርቅ በኋላ ላይ መጥቼ እወስደዋለው አለ። የንግሥ በዓሉ በመዝሙርና በጸሎት ተጠናቀቀ።

እናም ይህ ክፋት ያደረበት ሰው ሁሉም ሕዝበ ክርስቲያን ወደ ቤቱ ሔዶ ሲያልቅ ወደ ቤተክርስቲያኑ ለመሔድ በልቡ አሰበ። እርሱ ያሰበው ”ሰው ሳያየኝ ሔጄ ዘርፌ ሀብታም እሆናለው” ብሎ ነበር። ነገር ግን ከሰዓት ሰው ሁሉ ከሔደ በኋላ እየተጣደፈ ከኋላው ሰው አለ የለም እያለ መገስገስ ጀመረ። ከዚያም እንደምንም ብሎ ከገዳሙ ደረሰ። ከደረሰም በኋላ በጠዋት ከሕዝበ ክርስቲያኑ ሲሰበሰብ የዋለውን ስጦታ በድፍረት ሊሰርቅ ሲል ከየት መጣ ሳይባል አያ አንበሶ ከተፍ አለና ”ለእመቤታችን የተበረከትውን ስጦታ ልትወስድ መጣህን” ብሎ በሰው ቋንቋ ሲያናግረው ሰውየው በጣም ደነገጠ።

ድንጋጤው በሦስት ምክንያት ነበር። የመጀመሪያው አያ አንበሶን ማየቱ ፣ ሁለተኛው አያ አንበሶ በሰው ቋንቋ መናገሩና ሦስተኛው ደግሞ የእራሱ ሕሊና በፈጠረበት ጭንቀት ነበር። በጣም ከመደንገጡ የተነሣ መንቀጥቀጥ እና መንዘፍዘፍ ጀመረ። አያ አንበሶ ለሁለተኛ ጊዜ ”አንተ ሰው የእግዚአብሔርን ለእግዚአብሔር የተባለውን ቃል አስታውስ እንጂ” አለው።

ሰውየው ይበልጥ በመደንገጥ አምላኬ ይቅር በለኝ እያለ ከቅጥረ ቤተክርስቲያኑ ወጥቶ ፈረጠጠ። ልጆች እግዚአብሔር ቤቱን በእንስሳትም እንደሚጠብቅ ተመለከታችሁ። ልጆች እግዚአብሔርን እንጂ ሰውንም ሆነ ሌላውን ተደብቆ ክፋት ማድረግ ኃጥያት መሆኑን መረዳት አለባችሁ። እግዚአብሔርን ማሳዘን ጥሩ አይደለም ፣ እግዚአብሔርን የሚያሳዝኑ ሥራዎች በሙሉ መጥፎ መሆናቸውን መረዳት አለባችሁ።  

ንብ

ከእለታት አንድ ቀን የማያምኑ ሰዎች ቤተክርስቲያናችንን ለማጥፋት ያስቡና ለመስረቅ የሚመች ሰዓት እስከሚያገኙ ድረስ ይጠብቁ ነበር። ነገር ግን በቤተክርስቲያኑ አጸድ ውስጥ በሚገኝ ትልቅ ዛፍ ንቦች ይኖሩ ነበር። መጥፎ የሚያስቡ ሰዎች ካሉ ከቤተክርስቲያን ያባርራሉ። ይህን ድርጊት ማንም አያውቅም ነበር። ከዚያም ከዕለታት አንድ ቀን ቤተክርስቲያንን ለማጥፋት ተጠራርተው ቤተክርስቲያን ማፍረሻ አካፋ ፣ ዶማ እና ሌሎችም መሳሪያዎች ይዘው ወደ ቤተክርስቲያን መሔድ ጀመሩ። ወደ ቤተክርስቲያኑ ሲጠጉ ንቦቹ አንድ ጊዜ ወጥተው እየነደፉ አባረሯቸው። ንቦቹ ቅድስት ቤተክርስቲያንን ከአረማውያን ጠበቁ ማለት ነው። ልጆች ክፋትን የሚያስቡ ሰዎች በእግዚአብሔር የሚታዘዝ ቁጣ እንደሚደርስባቸው ተረዳችሁ? ወደ ቤተ እግዚአብሔር የሚመጡ በቅን ልቦና በንጹሕ ሕሊና እግዚአብሔርን የሚያስደስት ተግባር ለመፈጸም መሔድ እንዳለባቸው መረዳት ይገባችኋል።


የመስቀሉ ነገር ለምናምን ለእኛ የእግዚአብሔር ኃይል ነው ። (1ኛ ቆሮ 1፥18)

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን።

እንኳን ለጌታችን ለመድኃኒታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ የመስቀል በዓል በሰላም አደረሳችሁ።

በዲያቆን ዮሐንስ አያሌው

ቤተ ክርስቲያናችን በዓለ እግዚአብሔርን በማክበር ነገረ እግዚአብሔርን፤ በዓለ ቅዱሳንን በማክበር ነገረ ቅዱሳንን፤ በዓለ መስቀልን በማከበር ነገረ መስቀሉን ታስተምራለች። በበዓለ መስቀሉ እና በሌሎችም በመንፈሳዊ በዓላት አከባበሯ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሰማይ ላይ ደምቃ እንደምታበራ ፀሐይ ናት። ፀሐይ በጨለማው ሰማይ ላይ ብርሃኗን በመፈንጠቅ የቀን ብርሃንና ውበት እንደምትሰጥ ቤተ ክርስቲያናችንም መንፈሳዊ ብርሃኑ በጠፋበት ዓለም የክርስትና ጸጋዋን እያጎናጸፈች ለጨለማው ዓለም ታበራለች። መንፈሳዊ በዓላትን ማክበር ወንጌልን መስበክ ነው። የቀደሙት ክርስቲያኖች ወንጌልን እንደልብ መስማት በማይችሉበት ዘመን በሰሙት ጥቂት ቃለ እግዚአብሔር ከአምላካቸው ጋር ይገናኙ የነበሩት በዓለ መስቀልንና በዓለ ቅዱሳንን በማክበርና መታሰቢያቸውን በማድረግ ነበር። 

ቅዱስ ጳውሎስ የመስቀሉ ነገር በሚጠፉ ሰዎች ዘንድ ስንፍና ነውና፣ ለምንድነው ለእኛ የእግዚአብሔር ኃይል ነው (1ኛ ቆሮ 1፥18) ብሏል። መስቀል በዘመነ ኦሪት ክፉ ይባሉ ከነበሩትና በሐዲስ ኪዳን አምላካችን የሕይወት መገኛ ካደረጋቸው ነገሮች አንዱ ነው። እግዚአብሔር ኢየሱስ ክርስቶስ በመስቀሉ ላይ ተሰቅሎ ከጨለማው ዓለም አውጥቶናል። በመሆኑም ዛሬ መስቀል የብርሃን እና የድል ምልክት ነው። በኃጢአቱ ምክንያት ከአምላኩ እርቆ የነበረውን አዳምን በዲያብሎስ ግዞት ከሚደርስበት መከራ ክብር ምስጋና ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመስቀል ላይ ራሱን መሥዋዕት አድርጎ አድኖታል (ሉቃ. 22፥52)። በዚህም “ፈደየ እዳነ በመስቀሉ” በመስቀሉ እዳችንን ከፈለ እያልን እናመሰግነዋለን። ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ “በመስቀሉ ጥልን አጠፋ”(ኤፌ. 2፤16) ብሎ እንዳስረዳን መስቀል ዛሬም ጥልንና ጥፋትን የሚያመጡ ወንበዴዎች ሰይጣናት የሚጠፉበት ነው። “ከባላጋራችን የተነሳ በእዛዝ የተጻፈውን የዳችንን ደብዳቤ ደመሰሰልን፣ ከመካከላችንም አራቀው፣ በመስቀሉም ቸነከረው” (ቆላ. 2፤14) እንደተባለ ዛሬም ወንበዴዎች አጋንንትን በኃይሉ ቸንክረን አስረን በሰላም እንድንኖር የሚያስችለን ታላቁ የሰላማችን አምባ መስቀል ነው። መስቀል ኃይል፣ ጸወን (አምባ፣ መጠጊያ፣ መሸሸጊያ፣ ማምለጫ) ነው።

መስቀል ዓለሙ የተቀደሰበት ዛሬም የሚቀደስበት የቅድስናና መንፈሳዊ ሀብታት መገኛ መኾኑን ኢትዮጵያዊው ሊቅ ቅዱስ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ ውዳሴ መስቀል በተሰኘ መጽሐፋቸው ሲመሰክሩ “አማንኬ ይደሉ ከመ ይስቅሉ ለወልደ እግዚአብሔር እስመ በመስቀሉ ይቄድሶ ለዓለም” በእውነት ኢየሱስ ክርስቶስ ዓለሙን ይቀድሰው ዘንድ በመስቀል ላይ መሰቀሉ የተገባ ነበር። ይኽም የተገባ የኾነው ኢየሱስ ክርስቶስ እንደ አዳም በድሎ፤ እንደ ቃየል ገድሎ፤ እንደ ይሁዳ አታሎ ሳይሆን በመስቀሉ ዓለሙን ኹሉ ይቀድሰው ዘንድ ነው።” በማለት ርኩሳን ይሰቀሉበት የነበረውን የጥፋት መሳሪያ ዓለምን የሚቀድስ መንፈሳዊ የውጊያ መሳሪያ እንዳደረገው ገልጸውልናል። ሌሎች ሊቃውንትም “ወለእመ ኢተሰቅለ እመ ኢድኅነ ባይሰቀልስ ኖሮ ባልዳንን ነበር፣ በማለት የሚያስተምሩን ይህንን እውነት ገልጦ ለማስረዳት ነው።

ለቅዱስ መስቀሉ በዓሉን እንድናከብር ብቻ ሳይኾን የጸጋ ስግደት እንድንሰግድለትም ታዝዘናል። ይህንንም ያዘዙን ቅዱስ ወንጌልን ያስተማሩ ሐዋርያት መኾናቸውን ቤተ ክርስቲያናችን ትመሰክራለች። መስተብቍዕ ዘመስቀል በተባለው የቤተ ክርስቲያናችን የጸሎት ክፍል የተገለጠውን ስንመለከት “አዘዙነ መምህራ ቅዱስ ወንጌል አምሳለ ፈጣሪ ልዑል ንስግድ ለመስቀል ወለማርያም ድንግል ለማርያምሰ ዘንሰግድ ላቲ እስመ ነሥአ ሥጋ እም ሥጋሃ እግዚአብሔር ፈጣሪሃ ወረከብነ መድኃኒተ እምኔሃ ለዕፀ መስቀልኒ እስመ አንጠብጠበ ደመ ቃል” – የቅዱስ ወንጌል አስተማሪዎች ቅዱሳን ሐዋርያት/መምህራን ለድንግል ማርያምና ለመስቀል እንድንሰግድ አዘዙን። ለድንግል ማርያም የምሰግድላት እግዚአብሔር ከሥጋዋ ሥጋን ከነፍስዋም ነፍስን ነስቶ ሰው ስለኾነና ሰው በመኾኑም ከእርሷ መድኃኒትን ስላገኘን ነው። ለመስቀል የምንሰግደውም አካላዊ ቃል እግዚአብሔር ወልድ አዳኝ ፈራጅ የኾነ ቅዱስ ደሙን ስላንጠበጠበበት ነው ተብሎ ተብራርቶ ተጽፎልን  እናገኘዋለን። (መስተብቍዕ ዘመስቀል)

መስቀል ከላይ እንዳየነው በብሉይ ኪዳን ወንበዴዎች የሚቀጡበት መቀጣጫ የነበረ ቢኾንም የሐዲስ ኪዳን ሕይወትነቱን ለመግለጥ በዘመነ ኦሪትም ብዙ መንፈሳዊ ተአምራት ይፈጸሙበት ነበር። ለምሳሌ፦ በራፌድ በረሃ ሙሴ ከአማሌቃውያን ጋር በተዋጋ ጊዜ እጁን በትምእርተ መስቀል አምሳል በመዘርጋት አማሌቃውያንን ድል ነስቷቸዋል።(ዘጸ 17813) ስለዚህም “መሰቀል ዘተገብረ በአምሳሊሁ ለእደ ሙሴ በገዳመ ራፌድ በእንተ ጸብአ አማሌቅ” – በአማሌቃውያን ጥል ምክንያት በገዳመ ራፌድ በሙሴ እጆች አምሳል የተዘረጋ ቅዱስ መስቀል ነው ተብሎለታል። ሊቀ ነቢያት ሙሴ የማራን ውኃም እንጨት በመስቀል አምሳል አመሳቅሎ በመጣል ከመራራነቱ ፈውሶታል።(ዘጸ 152325) ይኸም “መስቀል ዘአጥዐሞ ለማይ መሪር በገዳመ ሱር ሶበ ተወደየ ውስቴቱ በእደ ሙሴ” በነብዩ በሙሴ እጅ ተመሳቅሎ ወደ ውስጡ በተጣለ ጊዜ መራራውን የሱር ውኃ ያጣፈጠው መስቀል ነው ተብሎለታል።(ውዳሴ መስቀል) የሱርን (የማራን) ውኃ እንዳጣፈጠ ዛሬም መስቀሉ የብዙዎችን መራራ ሕይወት ወደ መንፈሳዊ ጥፍጥና ይለውጣል። ነብዩ ሙሴ የሠራው የነሃስ እባብና መስቀሉም ዕፀ መስቀል እባብ የተባለ የሰይጣንን ተንኮል የምናልፍበት ከንክሻውም የምንድንበት መሆኑን ማሳያ ነው። በአጠቃላይ መስቀል ለክርስቲያኖች  ሕይወታችን ነው። በተጨማሪም መስቀል፦

  • ክርስቶስ የሚያበራበት ተቅዋመ ወርቅ (የወርቅ መቅረዝ) ነው።

ኢየሱስ ክርስቶስ “እኔ የለም ብርሃን ነኝ”። በብርሃኔ ተመላለሱ ብሎናል። ፀሐይ የሚሽከረከረው በነፋሳት እንደኾነ መብራት የሚበራውም በመቅረዝ (ማብሪያ) ላይ ኾኖ ነው። ኢየሱስ ክርስቶስ የዓለም ብርሃን ሲኾን ብርሃኑ የተገለጠበት ማብሪያው ደግሞ መስቀሉ ነው። ይህን ይዞ ሊቁ ሲያደንቅ “ኢየሱስ ክርስቶስን ሊሰቅሉት ሥጋውን ከልብስ አራቆቱት ምክንያቱም ለመብራት የሚፈልገው ኹሉ እንዲያየው ከፍ ብሎ በተቀመጠ በመቅረዙ ላይ ኾኖ ማብራት እንጅ በልብስ ተሸፍኖ መቀመጥ አይገባውምና፤ ዳግመኛም ሊሰቅሉ በእንጨት ላይ አወጡት ለምን ካላችኹ መብራትን አብርተው በተራራ ላይ እንጅ ከእንቅብ በታች በምድር ላይ ሊያስቀምጡት አይገባም።”  “ተቅዋምሰ መስቀል ውቱ ወማኅቶትኒ አማኑኤል ውቱ ናንሦሱ እንከ በብርሃኑ ለወልደ እግዚአብሔር ወኩሎ ዘየአምን ኪያሁ ውስተ ብርሃን ይሐውር ወጽልመትኒ ኢይረክቦ ማብሪያ መቅረዙ መስቀል ነው፤ በቀራንዮ ተራራ ላይ በተተከለ የመስቀሉ መቅረዝ ላይ የሚያበራው ብርሃን ደግሞ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። ይህንን ተረድተን ኹላችንንም በብርሃኑ እንመላለስ በእርሱም እንመን። በእርሱ የሚያምን በብርሃን ይመላለሳል ጨለማም አይቀርበውም በማለት አስተምሮናል። (ውዳሴ መስቀል)

  • አስቀድሞ የሰውን ልጅ ለማዳን የተዘጋጀ ነው።

አባ ጊዮርጊስ ሔዋን “ሔዋን” ተብላ ስም የወጣላት በእመቤታችን በቅድስት ድንግል አማካኝነት እንደኾነ ኹሉ በመስቀሉ ያመነ ሕይወት እንዲሆነው ስላወቀ መስቀሉንም አስቀድሞ “ዕፀ ሕይወት” አለው በማለት መስቀሉ አስቀድሞ በአምላክ ዘንድ ተዘጋጅቶ እንደነበር ይመሰክራሉ። የተሰቀለው እርሱ አስቀድሞ ባዘጋጀው መስቀል እንደኾነ ሲገልጡም “አምጽኡ ዘዚአሁ ለዚአሁ፣ የራሱን ለራሱ አመጡለት” በማለት እያደነቁ ጽፈዋል።

  • ድኅነታችን የተጻፈበት ሕያው መጽሐፍ ነው።

የዕዳ ደብዳቤያችን አስቀድሞ በእብነ እርካብ ተጽፎ ነበር። መጽሐፍ ድኅነታችን ደግሞ በአምላካችን በደሙ ቀለምነት በመስቀል ላይ ተጽፏል። ለዚህ ነው ቅዱስ ጳውሎስ “የዕዳ ደብዳቤያችንን በመስቀሉ ጠርቆ አስሮ ከመንገዳችን አስወገደው”ብሎ የመሰከረው። ሌላኛው ሊቅም “በንጠብጣበ ደምከ ተጽሕፈ ምሕረትከ በሰሌዳ መስቀልከ፣ በመስቀልህ ሰሌዳ ላይ በደምህ ነጠብጣብነት  ምሕረትህ ተጻፈች” በማለት ይህንን እውነት አጽንተው አስተምረዋል።

  • የአምላካችን የፍቅሩ መግለጫ ነው።

ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ለሰው ልጆች እንደ ክርስቶስ መስቀል ያለ የእግዚአብሔርን ፍቅር የሚያስረዳ (የሚገልጥ) ነገር የለም በማለት እንዳስረዳን፤ መስቀል የፍቅሩ መገለጫ ነው።( Commentary on 2nd Timothy) ቅዱስ ዮሐንስም “በወንጌሉ በእርሱ የሚያምን ኹሉ እንዲድን እንጅ እንዳይጠፋ እግዚአብሔር አንድያ ልጁን ቤዛ አድርጎ እስከ መስጠት ድረስ እንዲሁ ዓለሙን ወዶታል” በማለት የመሰከረለትን የእግዚአብሔር ፍቅር (ዮሐ. 316) ያለ መስቀሉ መረዳት አይቻልም። እስከ መስቀል ድረስ የታመነ ሆነ የተባለውን መረዳት የሚቻለው ነገረ መስቀሉ ሲገባን ብቻ ነው። ነገረ መስቀሉን ሳንረዳ ወደ እምነት ልንመጣ አንችልም። የመስቀልህ ጥላ ፈያታዊ ዘየማንን አንተን ወደ ማመን መለሰው እንዳለ ሊቁ ዛሬም ወደ ንስሐና ወደ ተግባራዊ ክርስትና የሚያደርሰን ትልቁ ሀብታችን በመስቀሉ ላይ የሚያበራው የክርስቶስ ብርሃን በልቡናችን ውስጥ ሲያበራ ነው።   

  • የሥጦታዎች ኹሉ መገኛ ነው።

ሕይወት፤ ድኅነት፤ ትንሣኤ፤ ምልጃ፤ እርቅ፤ ተስፋ፤ ተድላ ገነት በመስቀሉ የተገኙ ናቸው። እመቤታችንና ሐዋርያት ሁሉም የተሰጡን ከመስቀል ስር ነው። ከመስቀሉ ስር ካለቅስን አብሮን የሚያለቅስ አናጣም። ሌላው መስቀሉ ኃጢአታችንን በመግለጥ ወደ ንስሐ ያደርሰናል። ከመስቀሉ ስንርቅ ግን የአምላካችን ውለታውን እንረሳዋለን።

  • የዳግም ምጽአት ምልክታችን ነው።

ክርስቶስ በፍጻሜ ዘመን በኅልቀተ ዓለም የሚመጣው ምልክት እያሳየ ነው። ይህንንም ቅዱሳት መጽሐፍት ሲመሰክሩልን “ክርስቶስ ይመጽ በደመና ሰማይ ምስለ ኃይል ወመላእክቲሁ ምስሌሁ ወመስቀሉ ቅድሜሁ አሜሃ እለ ወግዑከ ይበክዩ፤ ወእለሰ ይነስዑ ማኅተመ ስምከ ይከውን ሎሙ ሰላመ ወሣህለ እግዚአብሔር ኢየሱስ ክርስቶስ ከኃይሉ ጋር መስቀሉ በፊቱ እያበራ በክበበ ትስብእት በይባቤ መላእክት ይመጣል፤ ያንጊዜም የወጉት ያለቅሳሉ፤ የስሙን ማኅተም የያዙ ግን ሰላምና የእግዚአብሔር ምሕረት ይደረግላቸዋል በማለት ያስተምራሉ። (ራዕ 17 ዘካ 121) አምላካችን እኛንም ለቀኝ ቁመት፣ ከእግዚአብሔር የሚሰጠውን ሰላምና ምሕረትም ለመቀበል የበቃን የሚያደርገን ምልክት መስቀል ነው።

በመሆኑም መስቀል በቤተ ክርስቲያን እንዲሁም በአባቶቻችን በካህናት እጅ ተይዞ ስናየው ክብሩና ኃይሉ እንደምናየው በሰውና በቦታ ብቻ የተወሰነ አይደለም። ምስጢሩና ሀብቱ ጥልቅና ብዙ ነው። ስለኾነም ድርሳን ተደርሶለታል፤ መልክእ፤ መስተበቍዕ፤ ውዳሴ፤ ሰላምና አርኬ ተጋጅቶለታል።(መጽሐፈ ጤፉት) በእነዚህ ድርሳናትም ሊቃውንቱ ደሙ የፈሰሰበት ክቡር መስቀልን ልብን ደስ የሚያሰኝ የሕይወት የወይን ወንዝ (ፈለገ ወይን)፤ መንፈሳዊ ጣዕምን የሚያሰጥ የማር ወንዝ (ፈለገ ማዕር)፤ ሕይወት የሚገኝበት፣ ነፍስን የሚያጠራና የሚያሰማምራት የመንፈሳዊ ዘይት ወንዝ (ፈለገ ቅብዕ)፤ በመንፈሳዊ ሕይወታችን ሕጻናት የኾን ሁሉ አባታችንን ወደ መምስል የሚያሳድገን በጸጋና በቅድስና የምንልቅበት የወተት ወንዝ (ፈለገ ሐሊብ)፣ እያሉ በሚያሰጠው ሀብትና ጸጋ ዓይነት እያመሰገኑ እንድናመሰግን አዝዘውናል።

በአጠቃላይ ቅዱስ ጳውሎስ “ነገር ግን ዓለም ለእኔ የተሰቀለበት እኔም ለዓለም ከተሰቀልኹበት ከኢየሱስ ክርስቶስ መስቀል ሌላ ትምክህት ከእኔ ይራቅ” እንዳለው፤ ትምክህታችን መስቀሉና በመስቀሉ ላይ የተገለጠው ፍቅር ኹኖ ዛሬም የቅዱስ መስቀልን መታሰቢያ ምክንያት በማድረግ ቃለ እግዚአብሔር በመስማት፤ ቅዳሴ በማስቀደስ፤ ዝክር በመዘከር መንፈሳዊ በረከት የምንቀበል ብዙዎቻችን ነን፤ ከዚህም በላይ የበረከት፤ የቃል ኪዳን፤ የማንነት ከዚህ አልፎም የሕልውናችን ምንጮች የሆኑ መንፈሳዊ በዓላታችንን በደማቅ ኹኔታ ማክበራችንን የበለጠ አጠንክረን ልንቀጥልበት የሚገባ ነው። የውጭው ጥቁር የባህል ደመና እንዳይወድቅባቸው፤ ከትውፊታዊ ይዘታቸውም ሳይቀነሱ እንዲከበሩ መጣርም ከምንፈጽማቸው ከእያንዳንዳችን የሚጠበቅ መንፈሳዊ ግዴታ ነው። ለዚህም ይረዳን ዘንድ እርስ በእርሳችን እንድንፋቀር፤ አምላካችንን፤ አገልግሎታችንን፤ ቤተ ክርስቲያናችንንና ሀገራችንን እንድንወድ የልዑል አምላካችን ቅዱስ ፈቃዱ ይኹንልን። አሜን!

 ወስብሐት ለእግዚአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ ክቡር ለዓለም ዓለም አሜን።